ዘዳግም 14:1-29

  • ሐዘንን ለመግለጽ ተብለው የሚደረጉ ተገቢ ያልሆኑ ነገሮች (1, 2)

  • ንጹሕ የሆነና ንጹሕ ያልሆነ ምግብ (3-21)

  • አንድ አሥረኛውን ለይሖዋ መስጠት (22-29)

14  “እናንተ የአምላካችሁ የይሖዋ ልጆች ናችሁ። ለሞተ ሰው ብላችሁ ሰውነታችሁን አትተልትሉ፤+ ቅንድባችሁንም* አትላጩ።+  ምክንያቱም አንተ ለአምላክህ ለይሖዋ ቅዱስ ሕዝብ ነህ፤+ ይሖዋም በምድር ላይ ካሉ ሕዝቦች ሁሉ መካከል አንተን የራሱ ሕዝብ፣ ልዩ ንብረቱ* እንድትሆን መርጦሃል።+  “ማንኛውንም አስጸያፊ ነገር አትብላ።+  የምትበሏቸው እንስሳት እነዚህ ናቸው፦+ በሬ፣ በግ፣ ፍየል፣  ርኤም፣ የሜዳ ፍየል፣ ድኩላ፣ የዱር ፍየል፣ አጋዘን፣ የዱር በግ እና የተራራ በግ።  ለሁለት የተከፈለ የተሰነጠቀ ሰኮና ያለውን እንዲሁም የሚያመሰኳውን ማንኛውንም እንስሳ መብላት ትችላላችሁ።  ሆኖም ከሚያመሰኩት ወይም የተሰነጠቀ ሰኮና ካላቸው እንስሳት መካከል እነዚህን አትብሉ፦ ግመል፣ ጥንቸልና ሽኮኮ፤ ምክንያቱም እነዚህ እንስሳት ቢያመሰኩም ሰኮናቸው ስንጥቅ አይደለም። እነሱ ለእናንተ ርኩስ ናቸው።+  አሳማም እንደዚሁ ነው፤ ምክንያቱም ሰኮናው ስንጥቅ ቢሆንም አያመሰኳም። ለእናንተ ርኩስ ነው። ሥጋቸውን መብላትም ሆነ በድናቸውን መንካት የለባችሁም።  “በውኃ ውስጥ ከሚኖሩ መካከል እነዚህን መብላት ትችላላችሁ፦ ክንፍና ቅርፊት ያላቸውን ሁሉ መብላት ትችላላችሁ።+ 10  ሆኖም ክንፍና ቅርፊት የሌለውን ማንኛውንም ነገር አትብሉ። ለእናንተ ርኩስ ነው። 11  “ንጹሕ የሆነውን ወፍ ሁሉ መብላት ትችላላችሁ። 12  እነዚህን ግን አትብሉ፦ ንስር፣ ዓሣ በል ጭላት፣ ጥቁር ጥምብ አንሳ፣+ 13  ቀይ ጭልፊትም ሆነ ጥቁር ጭልፊት እንዲሁም ሁሉንም ዓይነት ሌሎች ጭልፊቶች፣ 14  ማንኛውንም ዓይነት ቁራ፣ 15  ሰጎን፣ ጉጉት፣ ዓሣ አዳኝ ወፍ፣ ማንኛውንም ዓይነት ሲላ፣ 16  ትንሿ ጉጉት፣ ባለ ረጅም ጆሮ ጉጉት፣ ዝይ፣ 17  ሻላ፣ ጥምብ አንሳ፣ ለማሚት፣ 18  ራዛ፣ ማንኛውንም ዓይነት ሽመላ፣ ጅንጅላቴና የሌሊት ወፍ። 19  በተጨማሪም ክንፍ ያላቸው የሚርመሰመሱ ፍጥረታት* በሙሉ ለእናንተ ርኩስ ናቸው። መበላት የለባቸውም። 20  ንጹሕ የሆነን ማንኛውንም የሚበር ፍጥረት መብላት ትችላላችሁ። 21  “ሞቶ የተገኘን ማንኛውንም እንስሳ አትብሉ።+ ከዚህ ይልቅ በከተሞችህ* ውስጥ ለሚኖር የባዕድ አገር ሰው ልትሰጠውና እሱ ሊበላው ይችላል፤ አሊያም ለባዕድ አገር ሰው ሊሸጥ ይችላል። ምክንያቱም አንተ ለአምላክህ ለይሖዋ ቅዱስ ሕዝብ ነህ። “የፍየልን ጠቦት በእናቱ ወተት አትቀቅል።+ 22  “በየዓመቱ ከእርሻህ ላይ ከምታገኘው ምርት ሁሉ አንድ አሥረኛውን* መስጠት አለብህ።+ 23  ዘወትር አምላክህን ይሖዋን መፍራትን+ እንድትማር የእህልህን፣ የአዲስ የወይን ጠጅህንና የዘይትህን አንድ አሥረኛ እንዲሁም የከብትህንና የመንጋህን በኩራት በአምላክህ በይሖዋ ፊት ለስሙ ማደሪያ እንዲሆን በሚመርጠው ስፍራ ብላ።+ 24  “ሆኖም አምላክህ ይሖዋ ለስሙ ማደሪያ እንዲሆን የሚመርጠው ስፍራ+ አንተ ካለህበት ቦታ ሩቅ ከመሆኑ የተነሳ መንገዱ በጣም ቢረዝምብህና (አምላክህ ይሖዋ ስለባረከህ) እዚያ ድረስ ተሸክመኸው መሄድ ባትችል 25  ወደ ገንዘብ ልትቀይረው ትችላለህ፤ ገንዘቡንም ይዘህ አምላክህ ይሖዋ ወደሚመርጠው ስፍራ ሂድ። 26  ከዚያም በገንዘቡ የምትሻውን* ነገር ይኸውም ከብት፣ በግ፣ ፍየል፣ የወይን ጠጅ፣ ሌላ የሚያሰክር መጠጥና የሚያስደስትህን* ማንኛውንም ነገር መግዛት ትችላለህ፤ አንተና ቤተሰብህም በአምላክህ በይሖዋ ፊት በዚያ ብሉ፤ ተደሰቱም።+ 27  በከተሞችህ ውስጥ የሚኖረውን ሌዋዊ ችላ አትበለው፤+ ምክንያቱም እሱ ከአንተ ጋር ድርሻም ሆነ ውርሻ አልተሰጠውም።+ 28  “በየሦስት ዓመቱ መጨረሻ ላይ በዚያ ዓመት ያገኘኸውን ምርት አንድ አሥረኛ በሙሉ አምጥተህ በከተሞችህ ውስጥ አከማች።+ 29  አምላክህ ይሖዋ የእጅህን ሥራ ሁሉ እንዲባርክልህ+ ከአንተ ጋር ድርሻም ሆነ ውርሻ ያልተሰጠው ሌዋዊ እንዲሁም በከተሞችህ ውስጥ የሚኖሩት የባዕድ አገር ሰዎች፣ አባት የሌላቸው* ልጆችና መበለቶች መጥተው እስኪጠግቡ ድረስ ይብሉ።+

የግርጌ ማስታወሻዎች

ቃል በቃል “በዓይኖቻችሁ መካከል ያለውን ቦታ።” ግንባርን ሊጨምር ይችላል።
ወይም “ውድ ሀብቱ።”
ወይም “ነፍሳት።”
ቃል በቃል “በደጆችህ።”
ወይም “አሥራት።”
ወይም “ነፍስህ የምትሻውን።”
ወይም “ነፍስህ የምትጠይቅህን።”
ወይም “ወላጅ አልባ የሆኑ።”