የጴጥሮስ የመጀመሪያው ደብዳቤ 4:1-19

  • እንደ ክርስቶስ ለአምላክ ፈቃድ ኑሩ (1-6)

  • “የሁሉም ነገር መጨረሻ ቀርቧል” (7-11)

  • ክርስቲያን በመሆናችን የሚደርስብንን መከራ መቀበል (12-19)

4  ክርስቶስ በሥጋ መከራ ስለተቀበለ+ እናንተም ይህንኑ አስተሳሰብ* ለማንጸባረቅ ዝግጁ ሁኑ፤ ምክንያቱም በሥጋ መከራ የተቀበለ ሰው ኃጢአት መሥራት አቁሟል፤+  ይኸውም ከእንግዲህ ወዲህ በሥጋ በሚኖርበት ቀሪ ሕይወቱ ለሰው ፍላጎት ሳይሆን+ ለአምላክ ፈቃድ መኖር ይችል ዘንድ ነው።+  ማንአለብኝነት የሚንጸባረቅባቸው ድርጊቶች በመፈጸም፣* ልቅ በሆነ የሥጋ ፍላጎት፣ ከልክ በላይ በመጠጣት፣ መረን በለቀቀ ድግስ፣ በመጠጥ ግብዣዎችና በአስጸያፊ የጣዖት አምልኮ በመካፈል የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት+ ያለፈው ጊዜ ይበቃል።+  ይህን በመሰለው ያዘቀጠ ወራዳ ሕይወት ከእነሱ ጋር መሮጣችሁን ስለማትቀጥሉ ግራ ይጋባሉ፤ በመሆኑም ይሰድቧችኋል።+  ይሁንና እነዚህ ሰዎች በሕያዋንና በሙታን ላይ ሊፈርድ ለተዘጋጀው መልስ ይሰጣሉ።+  እንዲያውም ምሥራቹ ለሙታንም* የተሰበከው በዚህ ምክንያት ነው፤+ በመሆኑም ከሰው አመለካከት አንጻር በሥጋ የሚፈረድባቸው ቢሆንም ከአምላክ አመለካከት አንጻር ከመንፈስ ጋር በሚስማማ ሁኔታ መኖር ይችላሉ።  ሆኖም የሁሉም ነገር መጨረሻ ቀርቧል። ስለዚህ ጤናማ አስተሳሰብ ይኑራችሁ፤+ እንዲሁም በጸሎት ረገድ ንቁዎች ሁኑ።+  ከሁሉም በላይ አንዳችሁ ለሌላው የጠለቀ ፍቅር ይኑራችሁ፤+ ምክንያቱም ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናል።+  ሳታጉረመርሙ አንዳችሁ ለሌላው የእንግዳ ተቀባይነት መንፈስ አሳዩ።+ 10  በልዩ ልዩ መንገዶች የተገለጸው የአምላክ ጸጋ መልካም መጋቢዎች እንደመሆናችሁ መጠን፣ እያንዳንዳችሁ በተቀበላችሁት ስጦታ መሠረት የተሰጣችሁን ስጦታ አንዳችሁ ሌላውን ለማገልገል ተጠቀሙበት።+ 11  የሚናገር ማንም ቢኖር ከአምላክ የተቀበለውን ቃል እየተናገረ እንዳለ ሆኖ ይናገር፤ የሚያገለግል ማንም ቢኖር አምላክ በሚሰጠው ኃይል ተማምኖ ያገልግል፤+ ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ አማካኝነት አምላክ በሁሉም ነገር እንዲከበር ነው።+ ክብርና ኃይል ለዘላለም የእሱ ነው። አሜን። 12  የተወደዳችሁ ወንድሞች፣ እንደ እሳት ባሉ ከባድ ፈተናዎች ስትፈተኑ እንግዳ የሆነ ነገር እየደረሰባችሁ እንዳለ አድርጋችሁ በማሰብ አትደነቁ።+ 13  ከዚህ ይልቅ ክርስቶስ በክብሩ በሚገለጥበት ወቅት+ እናንተም እንድትደሰቱና እጅግ ሐሴት እንድታደርጉ እሱ የተቀበለው መከራ ተካፋዮች+ በመሆናችሁ ምንጊዜም ደስ ይበላችሁ።+ 14  ለክርስቶስ ስም ስትሉ ብትነቀፉ* ደስተኞች ናችሁ፤+ ምክንያቱም የክብር መንፈስ ይኸውም የአምላክ መንፈስ በእናንተ ላይ ያርፋል። 15  ይሁን እንጂ ከእናንተ መካከል ማንም ነፍሰ ገዳይ ወይም ሌባ ወይም ክፉ አድራጊ ወይም በሌሎች ሰዎች ጉዳይ ጣልቃ የሚገባ ሆኖ መከራ አይቀበል።+ 16  ይሁንና ማንም ሰው ክርስቲያን በመሆኑ መከራ ቢደርስበት ምንም ኀፍረት አይሰማው፤+ ይልቁንም ይህን ስም ተሸክሞ አምላክን ያክብር። 17  ፍርድ ከአምላክ ቤት+ የሚጀምርበት አስቀድሞ የተወሰነው ጊዜ ይህ ነውና። እንግዲህ ፍርድ በእኛ የሚጀምር ከሆነ+ ለአምላክ ምሥራች ታዛዥ ያልሆኑ ሰዎች መጨረሻ ምን ይሆን?+ 18  “እንግዲህ ጻድቅ በጭንቅ የሚድን ከሆነ ኃጢአተኛውና ፈሪሃ አምላክ የሌለው ሰውማ ምን ይውጠው ይሆን?”+ 19  ስለዚህ የአምላክን ፈቃድ በማድረጋቸው መከራ የሚደርስባቸው ሰዎች መልካም እያደረጉ ራሳቸውን* ታማኝ ለሆነው ፈጣሪ አደራ ይስጡ።+

የግርጌ ማስታወሻዎች

ወይም “ቆራጥ አቋም፤ ቁርጥ ውሳኔ።”
ወይም “እፍረተ ቢስነት በሚንጸባረቅበት ምግባር።” እዚህ ላይ የገባው አሴልጊያ የሚለው ግሪክኛ ቃል ብዙ ቁጥር ነው። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።
ይህ በመንፈሳዊ ሁኔታ ሙታን የሆኑትን ያመለክታል። ኤፌ 2:1ን ተመልከት።
ወይም “ብትሰደቡ።”
ወይም “ነፍሳቸውን።”