ዕዝራ 8:1-36

  • ከዕዝራ ጋር የተመለሱት ሰዎች ዝርዝር (1-14)

  • ለጉዞው የተደረገ ዝግጅት (15-30)

  • ከባቢሎን ተነስተው ኢየሩሳሌም ደረሱ (31-36)

8  በንጉሥ አርጤክስስ+ የግዛት ዘመን ከባቢሎን አብረውኝ የወጡት የአባቶች ቤት መሪዎች የዘር ሐረግ ዝርዝር ይህ ነው፦  ከፊንሃስ+ ልጆች ጌርሳም፣ ከኢታምር+ ልጆች ዳንኤል፣ ከዳዊት ልጆች ሃጡሽ፣  ከሸካንያህ ልጆች፣ ከፓሮሽ ልጆች ዘካርያስ እንዲሁም ከእሱ ጋር የተመዘገቡ 150 ወንዶች ነበሩ፤  ከፓሃትሞአብ+ ልጆች የዘራህያህ ልጅ የሆነው ኤሊየሆዔናይ እንዲሁም ከእሱ ጋር 200 ወንዶች፣  ከዛቱ+ ልጆች የያሃዚኤል ልጅ የሆነው ሸካንያህ እንዲሁም ከእሱ ጋር 300 ወንዶች፣  ከአዲን+ ልጆች የዮናታን ልጅ የሆነው ኤቤድ እንዲሁም ከእሱ ጋር 50 ወንዶች፣  ከኤላም+ ልጆች የጎቶልያ ልጅ የሆነው የሻያህ እንዲሁም ከእሱ ጋር 70 ወንዶች፣  ከሰፋጥያህ+ ልጆች የሚካኤል ልጅ የሆነው ዘባድያህ እንዲሁም ከእሱ ጋር 80 ወንዶች፣  ከኢዮዓብ ልጆች የየሂኤል ልጅ የሆነው አብድዩ እንዲሁም ከእሱ ጋር 218 ወንዶች፣ 10  ከባኒ ልጆች የዮሲፍያህ ልጅ የሆነው ሸሎሚት እንዲሁም ከእሱ ጋር 160 ወንዶች፣ 11  ከቤባይ+ ልጆች የቤባይ ልጅ የሆነው ዘካርያስ እንዲሁም ከእሱ ጋር 28 ወንዶች፣ 12  ከአዝጋድ+ ልጆች የሃቃጣን ልጅ የሆነው ዮሃናን እንዲሁም ከእሱ ጋር 110 ወንዶች፣ 13  ከአዶኒቃም+ ልጆች የመጨረሻዎቹ የሆኑት ስማቸው ኤሊፌሌት፣ የኢዔልና ሸማያህ ሲሆን ከእነሱም ጋር 60 ወንዶች፤ 14  ከቢግዋይ+ ልጆች ዑታይና ዛቡድ እንዲሁም ከእነሱ ጋር 70 ወንዶች። 15  እኔም ወደ አሃዋ+ በሚፈሰው ወንዝ አጠገብ ሰበሰብኳቸው፤ በዚያም ለሦስት ቀን ሰፈርን። ሆኖም ሕዝቡንና ካህናቱን ልብ ብዬ ስመለከት ከሌዋውያን መካከል ማንንም በዚያ አላገኘሁም። 16  በመሆኑም መሪዎች ለሆኑት ለኤሊዔዘር፣ ለአርዔል፣ ለሸማያህ፣ ለኤልናታን፣ ለያሪብ፣ ለኤልናታን፣ ለናታን፣ ለዘካርያስና ለመሹላም እንዲሁም ለአስተማሪዎቹ ለዮያሪብና ለኤልናታን መልእክት ላክሁባቸው። 17  ከዚያም ካሲፍያ በተባለው ቦታ መሪ ወደሆነው ወደ ኢዶ እንዲሄዱ አዘዝኳቸው። ኢዶንና በካሲፍያ የቤተ መቅደስ አገልጋዮች* የሆኑትን ወንድሞቹን በአምላካችን ቤት የሚያገለግሉ ሰዎችን ያመጡልን ዘንድ እንዲጠይቋቸው ነገርኳቸው። 18  መልካም የሆነው የአምላካችን እጅ በእኛ ላይ ስለነበር የእስራኤል ልጅ የሌዊ የልጅ ልጅ ከሆነው ከማህሊ+ ልጆች መካከል አስተዋይ የሆነውን ሸረበያህን፣+ ወንዶች ልጆቹንና ወንድሞቹን በአጠቃላይ 18 ሰዎችን አመጡልን፤ 19  እንዲሁም ሃሻብያህንና ከእሱም ጋር ከሜራራውያን+ መካከል የሻያህን፣ ወንድሞቹንና ወንዶች ልጆቻቸውን በአጠቃላይ 20 ሰዎችን አመጡልን። 20  በተጨማሪም ከቤተ መቅደሱ አገልጋዮች* መካከል ዳዊትና መኳንንቱ ሌዋውያኑ ለሚያቀርቡት አገልግሎት የሰጧቸው 220 ሰዎች ነበሩ፤ ሁሉም በየስማቸው ተመዝግበው ነበር። 21  ከዚያም ራሳችንን በአምላካችን ፊት ለማዋረድ እንዲሁም በጉዟችን ወቅት ለእኛም ሆነ ለልጆቻችንና ለንብረቶቻችን በሙሉ የሚሆን መመሪያ ከእሱ ለማግኘት እዚያው በአሃዋ ወንዝ ጾም አወጅኩ። 22  “መልካም የሆነው የአምላካችን እጅ እሱን በሚሹት ሁሉ ላይ ነው፤+ እሱን በሚተዉት ሁሉ ላይ ግን ኃይሉንና ቁጣውን ይገልጣል”+ በማለት ለንጉሡ ነግረነው ስለነበር በጉዟችን ላይ ከሚያጋጥሙን ጠላቶች የሚጠብቁን ወታደሮችና ፈረሰኞች እንዲሰጠን ንጉሡን መጠየቅ አፈርኩ። 23  ስለሆነም ጾምን፤ ይህን በተመለከተም ለአምላካችን ልመና አቀረብን፤ እሱም ልመናችንን ሰማ።+ 24  እኔም ከዋነኞቹ ካህናት መካከል 12ቱን ይኸውም ሸረበያህንና ሃሻብያህን+ እንዲሁም አሥር ወንድሞቻቸውን ለየሁ። 25  ከዚያም ንጉሡ፣ አማካሪዎቹና መኳንንቱ እንዲሁም በዚያ የተገኙት እስራኤላውያን በሙሉ ለአምላካችን ቤት የሰጡትን መዋጮ ማለትም ብሩን፣ ወርቁንና ዕቃዎቹን መዘንኩላቸው።+ 26  የሚከተሉትንም ዕቃዎች መዝኜ ሰጠኋቸው፦ 650 ታላንት* ብር፣ 2 ታላንት የሚመዝኑ 100 የብር ዕቃዎች፣ 100 ታላንት ወርቅ 27  እንዲሁም 1,000 ዳሪክ* የሚመዝኑ 20 ትናንሽ ጎድጓዳ የወርቅ ሳህኖችና የወርቅ ያህል ተፈላጊ የሆኑ ከሚያብረቀርቅ ጥሩ መዳብ የተሠሩ 2 ዕቃዎች። 28  ከዚያም እንዲህ አልኳቸው፦ “እናንተ ለይሖዋ የተቀደሳችሁ ናችሁ፤+ ዕቃዎቹም የተቀደሱ ናቸው፤ ብሩና ወርቁ ለአባቶቻችሁ አምላክ ለይሖዋ የቀረበ የፈቃደኝነት መባ ነው። 29  በኢየሩሳሌም በሚገኙት በይሖዋ ቤት ክፍሎች* ውስጥ በዋነኞቹ ካህናትና ሌዋውያን እንዲሁም በእስራኤል የአባቶች ቤት መኳንንት ፊት እስክትመዝኗቸው ድረስ በጥንቃቄ ጠብቋቸው።”+ 30  ካህናቱና ሌዋውያኑም የተመዘነላቸውን ብር፣ ወርቅና ዕቃ በኢየሩሳሌም ወደሚገኘው ወደ አምላካችን ቤት ለመውሰድ ተረከቡ። 31  በኋላም በመጀመሪያው ወር ከወሩም በ12ኛው ቀን+ ወደ ኢየሩሳሌም ለመሄድ ከአሃዋ+ ወንዝ ተነሳን፤ የአምላካችንም እጅ በላያችን ነበር፤ እሱም በመንገድ ላይ ከጠላት እጅና ከሽምቅ ጥቃት ታደገን። 32  ወደ ኢየሩሳሌም+ መጥተን በዚያ ለሦስት ቀን ተቀመጥን። 33  በአራተኛውም ቀን ብሩን፣ ወርቁንና ዕቃዎቹን በአምላካችን ቤት+ መዝነን ለዑሪያህ ልጅ ለካህኑ ለመሬሞት+ አስረከብነው፤ ከእሱም ጋር የፊንሃስ ልጅ አልዓዛር እንዲሁም ሌዋውያን የሆኑት የየሹዋ ልጅ ዮዛባድና+ የቢኑይ+ ልጅ ኖአድያህ ነበሩ። 34  እያንዳንዱም ነገር ተቆጥሮ ተመዘነ፤ ክብደቱም ሁሉ ተመዘገበ። 35  በግዞት ተወስደው የነበሩት ከምርኮ ነፃ የወጡ ሰዎች ለእስራኤል አምላክ የሚቃጠሉ መሥዋዕቶችን አቀረቡ፤ ለመላው እስራኤል 12 በሬዎችን፣+ 96 አውራ በጎችን፣+ 77 ተባዕት የበግ ጠቦቶችንና 12 ተባዕት ፍየሎችን+ የኃጢአት መባ አድርገው አቀረቡ፤ ይህ ሁሉ ለይሖዋ የቀረበ የሚቃጠል መባ ነበር።+ 36  ከዚያም ንጉሡ ያወጣቸውን ድንጋጌዎች+ ለንጉሡ የአውራጃ ገዢዎችና* ከወንዙ+ ባሻገር* ባለው ክልል ለሚገኙት ገዢዎች ሰጠናቸው፤ እነሱም ለሕዝቡና ለእውነተኛው አምላክ ቤት ድጋፍ ሰጡ።+

የግርጌ ማስታወሻዎች

ወይም “ናታኒሞች።” ቃል በቃል “የተሰጡ ሰዎች።”
ወይም “ከናታኒሞቹ።” ቃል በቃል “ከተሰጡት ሰዎች።”
አንድ ታላንት 34.2 ኪሎ ግራም ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ዳሪክ የፋርስ የወርቅ ሳንቲም ነበር። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ወይም “መመገቢያ አዳራሾች።”
ይህ የማዕረግ ስም “የግዛቱ ጠባቂዎች” የሚል ትርጉም ያለው ሲሆን እዚህ ላይ የተሠራበት በፋርስ ግዛት የሚገኙ የአውራጃ ገዢዎችን ለማመልከት ነው።
ወይም “ኤፍራጥስን ተሻግሮ።”