በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የይሖዋ ሥራዎች—ታላቅና ድንቅ ናቸው

የይሖዋ ሥራዎች—ታላቅና ድንቅ ናቸው

ምዕራፍ 31

የይሖዋ ሥራዎች—ታላቅና ድንቅ ናቸው

ራእይ 10--ራእይ 15:1 እስከ 16:21

ርዕሰ ጉዳይ:- ይሖዋ በመቅደሱ ውስጥ ነው፣ ሰባት የቁጣው ጽዋዎች በምድር ላይ ፈሰሱ

ራእዩ የሚፈጸምበት ጊዜ:- ከ1919 እስከ አርማጌዶን

1, 2. (ሀ) ዮሐንስ የሚነግረን የትኛውን ሦስተኛ ምልክት ነው? (ለ) ከጥንት ዘመን ጀምሮ የይሖዋ አገልጋዮች የትኛውን የመላእክት የሥራ ድርሻ ያውቁ ነበር?

ወንድ ልጅ የምትወልድ አንዲት ሴት ታየች! አንድ ትልቅ ዘንዶ ደግሞ ሕጻኑን ሊውጥ ተዘጋጅቶአል! እነዚህ በ⁠ራእይ ምዕራፍ 12 ላይ የተገለጹት ሁለት ሰማያዊ ምልክቶች በአምላክ ሴት ዘሮችና በሰይጣንና በአጋንንታዊ ዘሮቹ መካከል የኖረው ለብዙ ዘመናት የቆየ ግጭት ከፍተኛ ደረጃ ላይ መድረሱን አስገንዝበውን ነበር። ዮሐንስ የእነዚህን ምልክቶች ታላቅነት ሲገልጽልን “ታላቅም ምልክት በሰማይ ታየ። . . . ሌላም ምልክት በሰማይ ታየ” ብሎአል። (ራእይ 12:1, 3, 7-12) አሁን ደግሞ ዮሐንስ ሦስተኛ ምልክት ይነግረናል:- “ሌላም ታላቅና ድንቅ ምልክት በሰማይ አየሁ የእግዚአብሔር ቁጣ በእነርሱ ስለሚፈጸም ኋለኛዎቹን ሰባት መቅሠፍቶች የያዙ ሰባት መላእክት ታዩ።” (ራእይ 15:1) ይህ ሦስተኛ ምልክት ለይሖዋ አገልጋዮች የሚጠቅም መልእክት ይዞአል።

2 አሁንም መላእክት የአምላክን ፈቃድ በማስፈጸም ረገድ ያላቸውን ከፍተኛ ሚና ማስተዋል ይቻላል። ይህም የአምላክ አገልጋዮች ለብዙ ዘመናት የሚያውቁት ሐቅ ነው። የጥንቱ መዝሙራዊ እንኳን ስለ እነዚህ መላእክት ሲናገር “ቃሉን የምትፈጽሙ ብርቱዎችና ኃያላን የቃሉንም ድምፅ የምትሰሙ መላእክቱ ሁሉ እግዚአብሔርን [“ይሖዋ፣” NW] ባርኩ” ብሎአል። (መዝሙር 103:20) አሁን ደግሞ በዚህ አዲስ ትርዒት ውስጥ መላእክት የመጨረሻዎቹን ሰባት መቅሰፍቶች የማፍሰስ ሥራ ተሰጥቶአቸዋል።

3. ሰባቱ መቅሰፍቶች ምንድን ናቸው? የመቅሰፍቶቹስ መፍሰስ ምን ያመለክታል?

3 እነዚህ መቅሰፍቶች ምንድን ናቸው? እንደ ሰባቱ የመለከት ድምፆች ይሖዋ ስለዚህ ዓለም የተለያዩ ገጽታዎች ያለውን አመለካከት የሚያስታውቁና የፍርዱ ውሣኔ ስለሚያስከትለው የመጨረሻ ውጤት የሚያስጠነቅቁ መግለጫዎች ናቸው። (ራእይ 8:1 እስከ 9:21) የእነዚህ መቅሰፍቶች መፍሰስ የይሖዋ የቁጣ ዕቃዎች እሳታማ በሆነው የቁጣው ቀን በሚጠፉበት ጊዜ የሚፈጸመውን የቅጣት ፍርድ ያመለክታል። (ኢሳይያስ 13:9-13፤ ራእይ 6:16, 17) ስለዚህ ‘የአምላክ ቁጣ የሚፈጸመው’ በእነዚህ መቅሰፍቶች አማካኝነት ነው። ይሁን እንጂ ዮሐንስ ስለ መቅሰፍቶቹ መፍሰስ ከመናገሩ በፊት መቅሰፍቶቹ ስለማይጎዱአቸው ሰዎች ተናግሮአል። እነዚህ ታማኝ ሰዎች የአውሬውን ምልክት ለመቀበል እምቢተኞች ስለሆኑ የይሖዋን የቁጣ ቀን እያወጁ የውዳሴ መዝሙር ይዘምሩለታል።—ራእይ 13:15-17

የሙሴና የበጉ መዝሙር

4. አሁን ዮሐንስ ምን ነገር ተመለከተ?

4 አሁን ዮሐንስ በጣም አስደናቂ የሆነ ትዕይንት ተመለከተ:- “በእሳትም የተቀላቀለውን የብርጭቆ ባሕር የሚመስለውን አየሁ፣ በአውሬውና በምስሉም በስሙም ቁጥር ላይ ድል ነሥተው የነበሩት የእግዚአብሔርን በገና ይዘው በብርጭቆ ባሕር ላይ ሲቆሙ አየሁ።”—ራእይ 15:2

5. “እሳት የተቀላቀለበት የብርጭቆ ባሕር” የምን ምሳሌ ነው?

5 “የብርጭቆው ባሕር” ዮሐንስ ቀደም ሲል በይሖዋ ዙፋን ፊት ተመልክቶት ከነበረው ባሕር ጋር አንድ ነው። (ራእይ 4:6) በሰሎሞን ቤተ መቅደስ ውስጥ ካህናቱ ራሳቸውን ለማጽዳት የሚያስፈልጋቸውን ውኃ ይቀዱበት ከነበረው “ክብ ኩሬ” ጋር ይመሳሰላል። (1 ነገሥት 7:23) ስለዚህ ኢየሱስ የቅቡዓን ክርስቲያኖችን የካህናት ጉባኤ የሚያጠራበትን “የመታጠቢያ ውኃ” ወይም የአምላክ ቃል ማመልከቱ ተገቢ ነው። (ኤፌሶን 5:25, 26፤ ዕብራውያን 10:22) ይህ እንደ ብርጭቆ ያለ ባሕር ‘እሳት የተቀላቀለበት’ መሆኑ ደግሞ እነዚህ ቅቡዓን ክርስቲያኖች የወጡላቸውን ከፍተኛ የጽድቅ ደረጃዎች በሚታዘዙበት ጊዜ በከባድ ፈተናዎች ተፈትነው እንደሚጣሩ ያመለክታል። ከዚህም በላይ በአምላክ ቃል ውስጥ በአምላክ ጠላቶች ላይ የሚፈጸሙ እሳታማ ፍርዶች የሚገኙ መሆናቸውን ያመለክታል። (ዘዳግም 9:3፤ ሶፎንያስ 3:8) ከእነዚህ እሳታማ ፍርዶች አንዳንዶቹ አሁን ሊፈሱ በተዘጋጁት የመጨረሻ ሰባት መቅሰፍቶች ተገልጸዋል።

6. (ሀ) በሰማያዊው የብርጭቆ ባሕር ፊት የቆሙት መዘምራን እነማን ናቸው? ይህንንስ እንዴት እናውቃለን? (ለ) ድል የነሱትስ በምን መንገድ ነው?

6 በሰሎሞን ቤተ መቅደስ ውስጥ የነበረው “ክብ ኩሬ” ካህናቱ የሚገለገሉበት መሆኑ በሰማያዊው ብርጭቆ የሚመስል ባሕር ፊት የቆሙት መዘምራን ካህናት መሆናቸውን ያመለክታል። በእጆቻቸውም ‘የእግዚአብሔርን በገና’ ይዘዋል። ስለዚህ እነዚህ መዘምራን ከ24ቱ ሽማግሌዎችና ከ144,000ዎቹ የተለዩ አይደሉም። ምክንያቱም እነዚህም በበገና ድምፅ እየታጀቡ እንደሚዘምሩ ተገልጾአል። (ራእይ 5:8፤ 14:2) ዮሐንስ የተመለከታቸው መዘምራን “በአውሬውና በምስሉም በስሙም ቁጥር ላይ ድል” የነሱ ናቸው። ስለዚህ በመጨረሻው ቀን በምድር ላይ የሚኖሩት የ144,000 ክፍል አባሎች መሆን ይኖርባቸዋል። በቡድን ደረጃ በድል አድራጊነት ይወጣሉ። ከ1919 ጀምሮ ባሉት ወደ 90 የሚጠጉ ዓመታት የአውሬውን ምልክት ለመቀበልም ሆነ የአውሬው ምስል የሰው ልጅ ብቸኛ የሰላም ተስፋ መሆኑን ለማመን እምቢተኞች ሆነዋል። ከእነዚህ ሰዎች መካከል ብዙዎቹ እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ታማኝነታቸውን ጠብቀዋል። በሰማይ ላይ ሆነውም ገና በምድር ላይ የሚኖሩት ወንድሞቻቸው የሚያሰሙትን ዝማሬ በታላቅ ደስታ ይከታተላሉ።—ራእይ 14:11-13

7. በገና በጥንትዋ እስራኤል እንዴት ያገለግል ነበር? ዮሐንስ በተመለከተው ራእይ ውስጥ የአምላክ በገና መታየቱ እንዴት ሊነካን ይገባል?

7 እነዚህ ታማኝ ድል አድራጊዎች የአምላክን በገና ይዘዋል። በዚህ ረገድ ይሖዋን በበገና ድምፅ በታጀበ ዝማሬ ያመልኩ የነበሩትን የጥንት ሌዋውያን ይመስላሉ። አንዳንዶች ደግሞ የበገና ሙዚቃ እየሰሙ ትንቢት ተናግረው ነበር። (1 ዜና 15:16፤ 25:1-3) በጣም ውብ የነበረው የበገና ድርደራ እሥራኤላውያን ለይሖዋ የሚያቀርቡትን የደስታ፣ የውዳሴ ጸሎትና የምሥጋና ዝማሬ ያስውብና ያዳምቅ ነበር። (1 ዜና 13:8፤ መዝሙር 33:2፤ 43:4፤ 57:7, 8) በሐዘንና በግዞት ዘመናት የበገና ድምፅ አይሰማም ነበር። (መዝሙር 137:2) በዚህ ራእይ ውስጥ የአምላክ በገናዎች መታየታቸው ለአምላካችን የውዳሴና የምሥጋና የድል አድራጊነትና የፍሥሐ መዝሙር እንዲዘመር የሚሰማንን ናፍቆት የሚያረካ ነው። *

8. አሁን በመዘመር ላይ ያለው የትኛው መዝሙር ነው? የመዝሙሩስ ቃላት ምን የሚሉ ናቸው?

8 ዮሐንስም ቀጥሎ የሚገልጽልን ይህንን ነው። “ሁሉን የምትገዛ ጌታ [“ይሖዋ፣” NW] አምላክ ሆይ፣ ሥራህ ታላቅና ድንቅ ነው የአሕዛብ ንጉሥ ሆይ መንገድህ ጻድቅና እውነተኛ ነው ጌታ [“ይሖዋ፣” NW] ሆይ፣ የማይፈራህና ስምህንም የማያከብር ማን ነው? አንተ ብቻ ቅዱስ [“ታማኝ፣” NW] ነህና፣ የጽድቅም ሥራህ ስለ ተገለጠ አሕዛብ ሁሉ ይመጣሉ በፊትህም ይሰግዳሉ እያሉ የእግዚአብሔርን ባሪያ የሙሴን ቅኔና የበጉን ቅኔ ይዘምራሉ።”—ራእይ 15:3, 4

9. መዝሙሩ በከፊል የሙሴ መዝሙር የተባለው ለምንድን ነው?

9 እነዚህ ድል አድራጊዎች “የሙሴን ቅኔ” ማለትም ሙሴ ተመሳሳይ ሁኔታ አጋጥሞት በነበረበት ጊዜ ከዘመረው መዝሙር ጋር የሚመሳሰል መዝሙር ይዘምራሉ። እሥራኤላውያን በግብጽ ላይ የወረዱትን አሥር መቅሰፍቶችና የግብጻውያን ሠራዊት በቀይ ባሕር ውስጥ ሰጥሞ ሲጠፋ ከተመለከቱ በኋላ በሙሴ እየተመሩ “እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] ለዘላለሙ እስከ ፍጻሜ ይነግሣል” የሚለውን የውዳሴና የድል አድራጊነት መዝሙር አሰምተዋል። (ዘጸአት 15:1-19) በዮሐንስ ራእይ ውስጥ የታዩትም መዘምራን በተመሳሳይ ሁኔታ በአውሬው ላይ ድል ከተቀዳጁና ሰባቱን የመጨረሻ መቅሰፍቶች ካወጁ በኋላ ለዘላለሙ ንጉሥ የውዳሴ መዝሙር ማቅረባቸው ተገቢ ነው።—1 ጢሞቴዎስ 1:17

10. ሙሴ የደረሰው ሌላ መዝሙር የትኛው ነው? የዚህስ መዝሙር የመጨረሻ ቁጥር እጅግ ብዙ ሰዎችን የሚመለከት የሚሆነው እንዴት ነው?

10 አረጋዊው ሙሴ የእስራኤል ሕዝብ የከነዓንን ምድር ለመውረር ዝግጁ ሆኖ ይጠባበቅ በነበረበት ጊዜ በደረሰው መዝሙር “የእግዚአብሔርን [“የይሖዋ፣” NW] ስም እጠራለሁና ለአምላካችን ታላቅነትን ስጡ” በማለት ለሕዝቡ ተናግሮ ነበር። በተጨማሪም የዚህ መዝሙር የመጨረሻ ስንኝ እስራኤላውያን ላልሆኑ ሰዎች የማበረታቻ መልእክት አስተላልፎ ነበር። በመንፈስ የተጻፈው የሙሴ ቃል በዚህ ዘመን ለሚኖሩት እጅግ ብዙ ሰዎችም ደርሶአል። “እናንተ አሕዛብ ሆይ፣ ከሕዝቡ ጋር ደስ ይበላችሁ” አለ። ይሁን እንጂ ደስ የሚላቸው ለምንድን ነው? ይሖዋ “የባሪያዎቹን ደም ይበቀላልና፣ ጠላቶቹንም ይበቀላቸዋል።” የይሖዋ የጽድቅ ፍርድ በዚህ ዓይነት መፈጸሙ በይሖዋ ለሚታመኑ ሁሉ ደስታ ያመጣላቸዋል።—ዘዳግም 32:3, 43፤ ሮሜ 15:10-13፤ ራእይ 7:9

11. ዮሐንስ የሰማው መዝሙር መፈጸሙን የቀጠለው እንዴት ነው?

11 ሙሴ ራሱ በዚህ በጌታ ቀን ቢኖርና ከሰማያዊው የመዘምራን ጓድ ጋር “አሕዛብ ሁሉ ይመጣሉ፣ በፊትህም ይሰግዳሉ” ብሎ ቢዘምር ኖሮ ምንኛ ደስ ይለው ነበር! ይህ አንጸባራቂ መዝሙር ወደ ይሖዋ ምድራዊ ድርጅት በመጉረፍ ላይ ያሉትን በሚልዮን የሚቆጠሩ “አሕዛብ” በራእይ ብቻ ሳይሆን በእውን በምንመለከትበት በአሁኑ ጊዜ በመፈጸም ላይ ነው።

12. የድል አድራጊዎቹ መዝሙር “የበጉ መዝሙር” የተባለው ለምንድን ነው?

12 ይሁን እንጂ ይህ መዝሙር የሙሴ ብቻ ሳይሆን የበጉም መዝሙር ነው። እንዴት ቢባል ሙሴ ለእስራኤላውያን የተላከ የይሖዋ ነቢይ ሲሆን ይሖዋ እንደእርሱ ያለ ነቢይ ከመካከላቸው እንደሚያስነሳላቸው ትንቢት ተናግሮ ነበር። ይህም ነቢይ በጉ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆነ። ሙሴ “የአምላክ ባሪያ” ሲሆን ኢየሱስ ግን የአምላክ ልጅ ነበር። ስለዚህ ከሙሴ የሚበልጥ ነቢይ ነበር። (ዘዳግም 18:15-19፤ ሥራ 3:22, 23፤ ዕብራውያን 3:5, 6) ስለዚህ መዘምራኑ “የበጉንም ቅኔ” ጭምር ይዘምራሉ።

13. (ሀ) ኢየሱስ ከሙሴ የሚበልጥ ቢሆንም እንደ ሙሴ ያለ ነቢይ የሆነው እንዴት ነው? (ለ) ከመዘምራኑ ጋር ልንተባበር የምንችለው እንዴት ነው?

13 ኢየሱስ እንደ ሙሴ የአምላክን ውዳሴ ዘምሮአል፣ በጠላቶቹም ላይ ስለሚቀዳጃቸው ድሎች ትንቢት ተናግሮአል። (ማቴዎስ 24:21, 22፤ 26:30፤ ሉቃስ 19:41-44) በተጨማሪም ኢየሱስ አሕዛብ በሙሉ ይሖዋን ሊያወድሱ የሚመጡበትን ጊዜ በቅድሚያ ተመልክቶ ነበር። ራሱን መስዋዕት ያደረገ “የእግዚአብሔር በግ” እንደመሆኑ መጠን ይህን ውጤት ለማስገኘት ሲል ሕይወቱን አሳልፎ ሰጥቶአል። (ዮሐንስ 1:29፤ ራእይ 7:9፤ ከ⁠ኢሳይያስ 2:2-4⁠ና ከ⁠ዘካርያስ 8:23 ጋር አወዳድር።) ሙሴ የይሖዋን ስም ታላቅነት ለመገንዘብና ለማድነቅ እንዲሁም ስሙን ከፍ ለማድረግ እንደቻለ ሁሉ ኢየሱስም የይሖዋን ስም አሳውቆአል። (ዘጸአት 6:2, 3፤ መዝሙር 90:1, 17፤ ዮሐንስ 17:6) ይሖዋ የታመነ አምላክ ስለሆነ የተስፋ ቃሎቹ እንደሚፈጸሙ የተረጋገጠ ነው። ስለዚህ “ጌታ [“ይሖዋ፣” NW] ሆይ:- የማይፈራህና ስምህን የማያከብር ማን ነው?” የሚሉትን የመዝሙር ቃላት በማሰማት ከእነዚህ ታማኝ መዘምራን፣ ከበጉና ከሙሴ ጋር እንተባበራለን።

ጽዋዎች የያዙ መላእክት

14. ዮሐንስ ከመቅደሱ ሲወጡ የተመለከተው እነማንን ነው? ለእነርሱስ ምን ተሰጣቸው?

14 የእነዚህን ቅቡዓን ድል አድራጊዎች መዝሙር መስማታችን ተገቢ ነው። ለምን ቢባል የአምላክ ቁጣ በሞላባቸው ጽዋዎች ውስጥ የሚገኘውን ፍርድ በመላው ምድር ላይ አሳውቀዋል። ይሁን እንጂ ዮሐንስ ቀጥሎ እንደሚገልጸው በእነዚህ ጽዋዎች መፍሰስ ሥራ የሚካፈሉት ሰዎች ብቻ አይደሉም። “ከዚህም በኋላ አየሁ፣ የምስክርም ድንኳን መቅደስ በሰማይ ተከፈተ፣ ሰባቱንም መቅሠፍት የያዙ ሰባቱ መላእክት ከመቅደሱ ወጡ፤ ከተልባ እግርም የተሠራ ጥሩ የጌጥ ልብስ ለበሱ ደረታቸውንም በወርቅ መታጠቂያ ታጠቁ። ከአራቱም እንስሶች አንዱ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ የሚኖር የእግዚአብሔር ቁጣ የሞላባቸውን ሰባት የወርቅ ጽዋዎች ለሰባቱ መላእክት ሰጣቸው።”—ራእይ 15:5-7

15. ሰባቱ መላእክት ከመቅደሱ መውጣታቸው ሊያስደንቀን የማይገባው ለምንድን ነው?

15 የሰማያዊ ነገሮች ጥላ ወደ ነበረው የእስራኤላውያን ቤተ መቅደስ ቅድስተ ቅዱሳን ወይም እዚህ ላይ “መቅደስ” ወደተባለው ስፍራ ሊገባ የሚችለው ሊቀ ካህናቱ ብቻ ነበር። (ዕብራውያን 9:3, 7) ይህ ሥፍራ ይሖዋ የሚገኝበትን ሰማያዊ ቦታ ያመለክታል። ይሁን እንጂ በሰማይ ወደ ይሖዋ ዙፋን የመቅረብ መብት ያለው ሊቀ ካህናቱ ኢየሱስ ብቻ ሳይሆን መላእክቱ ጭምር ናቸው። (ማቴዎስ 18:10፤ ዕብራውያን 9:24-26) ስለዚህ በሰማይ ከሚገኘው መቅደስ ሰባት መላእክት ሲወጡ መታየታቸው ሊያስገርመን አይገባም። ይሖዋ አምላክ ራሱ የእርሱ ቁጣ የሞላባቸውን ጽዋዎች እንዲያፈስሱ አዝዞአቸዋል።—ራእይ 16:1

16. (ሀ) ሰባቱ መላእክት ለሥራቸው ሙሉ ብቃት ያላቸው መሆኑን የሚያሳየን ምንድን ነው? (ለ) ምሳሌያዊ ጽዋዎቹን በማፍሰስ ሥራ የሚካፈሉ ሌሎች ክፍሎችም እንዳሉ የሚያመለክተን ምንድን ነው?

16 እነዚህ መላእክት የተሰጣቸውን ሥራ ለመፈጸም ሙሉ ብቃት አላቸው። ብሩሕ የሆነ ንጹሕ ልብስ መልበሳቸው በይሖዋ ፊት መንፈሳዊ ንጽሕናና ቅድስና እንዳላቸው ያመለክታል። በተጨማሪም የወርቅ መታጠቂያ አድርገዋል። አንድ ሰው መታጠቂያ የሚያደርገው አንድ ዓይነት የሚሠራ ሥራ ሲኖረው ነው። (ዘሌዋውያን 8:7, 13፤ 1 ሳሙኤል 2:18፤ ሉቃስ 12:37፤ ዮሐንስ 13:4, 5) ስለዚህ መላእክቱ አንድ ዓይነት ሥራ ለመፈጸም ታጥቀዋል። ከዚህም በላይ ያደረጉት መታጠቂያ የወርቅ መታጠቂያ ነው። በጥንቱ ቤተ መቅደስ ውስጥ ወርቅ መለኮታዊና ሰማያዊ ነገሮችን ያመለክት ነበር። (ዕብራውያን 9:4, 11, 12) ይህም ማለት እነዚህ መላእክት መሥራት የሚኖርባቸው ውድና መለኮታዊ ሥራ አላቸው ማለት ነው። በዚህ ታላቅ ሥራ የተሰማሩ ሌሎች ፍጥረታትም አሉ። ከአራቱ ሕያዋን ፍጥረታት አንዱ ጽዋዎቹን ሰጣቸው። ይኸኛው ሕያው ፍጥረት የይሖዋን ፍርድ ለማወጅ የሚያስፈልገውን የድፍረትና የአይበገሬነት ባሕርይ የሚያመለክተውን አንበሳ የሚመስለው የመጀመሪያው ሕያው ፍጥረት ነው።—ራእይ 4:7

ይሖዋ በመቅደሱ ውስጥ ሆኖ

17. ዮሐንስ ስለ መቅደሱ ምን ይነግረናል? ይህስ በጥንትዋ እስራኤል የነበረውን መቅደስ የሚያሳስበን እንዴት ነው?

17 በመጨረሻም ዮሐንስ ይህንን የራእይ ክፍል ሲያጠቃልል እንዲህ አለ:- “ከእግዚአብሔርም ክብርና ከኃይሉ ጢስ በመቅደሱ ሞላበት፣ የሰባቱም መላእክት ሰባቱ መቅሰፍት እስኪፈጸሙ ድረስ አንድ እንኳ ወደ መቅደሱ ይገባ ዘንድ አልቻለም።” (ራእይ 15:8) በእስራኤል ታሪክ ውስጥ መቅደሱ በደመና የተሸፈነበትና ይህ የይሖዋ ክብር መግለጫ ካህናቱ ወደ ውስጥ እንዳይገቡ ያገደበት ጊዜ ነበር። (1 ነገሥት 8:10, 11፤ 2 ዜና 5:13, 14፤ ከኢሳይያስ 6:4, 5 ጋር አወዳድር።) እነዚህ ጊዜያት ይሖዋ በምድር ላይ የሚከናወኑ ነገሮችን በቅርብ ይከታተል የነበረባቸው ጊዜያት ነበሩ።

18. ሰባቱ መላእክት ለይሖዋ ሪፖርት ለማድረግ መቼ ይመለሳሉ?

18 በአሁኑም ጊዜ ይሖዋ በምድር ላይ የሚከናወኑ ነገሮችን በቅርብ ይከታተላል። ሰባቱ መላእክት የተሰጣቸውን ሥራ አጠናቅቀው እንዲጨርሱ ይፈልጋል። ይህ ጊዜ በ⁠መዝሙር 11:4-6 ላይ እንደተገለጸው ወሳኝ ፍርድ የሚሰጥበት ጊዜ ነው። “እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] በተቀደሰው መቅደሱ ነው፤ እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] ዙፋኑ በሰማይ ነው፤ ዓይኖቹ ወደ ድሀ ይመለከታሉ። ቅንድቦቹም የሰው ልጆችን ይመረምራሉ። እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] ጻድቅንና ኃጥእን ይመረምራል፤ ዓመፃን የወደዳት ግን ነፍሱን ጠልቶአል። ወጥመድ በኃጥአን ላይ ያዘንባል፣ እሳትና ዲን ዐውሎ ነፋስም የጽዋቸው እድል ፈንታ ነው።” እነዚህ ሰባት መቅሰፍቶች በክፉዎች ላይ ከመዝነባቸው በፊት ሰባቱ መላእክት ወደ ይሖዋ የከበሬታ ወንበር አይመለሱም።

19. (ሀ) ምን ትዕዛዝ ተሰጥቶአል? ትዕዛዙንስ ያስተላለፈው ማን ነው? (ለ) ምሳሌያዊው የይሖዋ ጽዋ መፍሰስ የጀመረው መቼ መሆን ይኖርበታል?

19 ታላቁ አስፈሪ ትዕዛዝ እንደ ነጎድጓድ ተሰማ:- “ለሰባቱም መላእክት:- ሄዳችሁ የእግዚአብሔርን ቁጣ ጽዋዎች በምድር ውስጥ አፍስሱ የሚል ታላቅ ድምፅ ከመቅደሱ ሰማሁ።” (ራእይ 16:1) ይህን ትዕዛዝ የሰጠው ማን ነው? የይሖዋ የግርማው ድምቀትና ኃይል ማንም ወደ መቅደሱ እንዳይገባ አግዶ ስለነበረ ትዕዛዙን የሰጠው ይሖዋ ራሱ መሆን ይኖርበታል። ይሖዋ ወደ መንፈሳዊ ቤተ መቅደሱ ለፍርድ የመጣው በ1918 ነበር። (ሚልክያስ 3:1-5) የአምላክ የቁጣው ጽዋ እንዲፈስ ያዘዘው ከዚህ በኋላ ባለው ጊዜ መሆን ይኖርበታል። እንዲያውም በእነዚህ ምሳሌያዊ ጽዋዎች ውስጥ የሚገኘው ፍርድ በተፋፋመ ሁኔታ መታወጅ የጀመረው በ1922 ነበር። በዛሬው ጊዜም ይህ የእወጃ ሥራ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሶአል።

ጽዋዎቹና የመለከት ድምፆች

20. የይሖዋ የቁጣ ጽዋዎች ስለ ምን ነገር ያስታውቃሉ? የሚፈስሱትስ እንዴት ነው?

20 የይሖዋ የቁጣ ጽዋዎች የተለያዩ የዓለም ክፍሎች በይሖዋ አመለካከት ምን መስለው እንደሚታዩ የሚገልጹና ይሖዋ ስለሚያመጣባቸው የቅጣት ፍርድ ማስጠንቀቂያ የሚሰጡ ናቸው። መላእክቱ ጽዋውን የሚያፈስሱት የሙሴንና የበጉን መዝሙር በሚዘምሩት የቅቡዓን ክርስቲያኖች ጉባኤ መሣሪያነት ነው። የዮሐንስ ክፍል አባሎች የመንግሥቱን ምሥራች እያወጁ እነዚህ የቁጣ ጽዋዎች የያዙአቸውን የፍርድ መልእክቶች በድፍረት አስታውቀዋል። (ማቴዎስ 24:14፤ ራእይ 14:6, 7) ስለዚህ መልእክታቸው ለሰው ልጅ ነፃነትን የሚያበስር የሰላም መልእክት እንዲሁም የአምላካችንን የበቀል ቀን የሚያውጅ የጦርነት መልእክት በመሆኑ ሁለት ዓይነት ገጽታ ያለው መልእክት ነው።—ኢሳይያስ 61:1, 2

21. የመጀመሪያዎቹ አራት የአምላክ ቁጣ ጽዋዎች ዒላማ ከመጀመሪያዎቹ አራት የመለከት ድምፆች ዒላማዎች ጋር አንድ የሆኑት እንዴት ነው? የሚለያዩትስ እንዴት ነው?

21 የመጀመሪያዎቹ አራት የአምላክ ቁጣ ጽዋዎች ዒላማ ከመጀመሪያዎቹ አራት የመለከት ድምፆች ዒላማ ጋር ተመሳሳይ ነው። ዒላማዎቹ ምድር፣ ባሕር፣ የውኃ ምንጮችና ወንዞች፣ እንዲሁም የሰማያዊ ብርሃናት ምንጮች ናቸው። (ራእይ 8:1-12) ይሁን እንጂ የመለከቶቹ ድምፆች በ“ሲሶው” ላይ መቅሰፍት እንደሚወርድ ሲያስታውቁ በአምላክ የቁጣ ጽዋ መፍሰስ የተጎዳው ግን ሙሉው ክፍል ነው። ስለዚህ በጌታ ቀን የመጀመሪያውን ትኩረት ያገኘችው ሕዝበ ክርስትና ብትሆንም ከይሖዋ የቁጣ ፍርድ መልእክቶች ሊያመልጥ የቻለ የሰይጣን ድርጅት ክፍል የለም።

22. የመጨረሻዎቹ ሦስት የመለከት ድምፆች የሚለዩት በምን ረገድ ነው? ከመጨረሻዎቹ ሦስት የይሖዋ ቁጣ ጽዋዎች ጋር የሚመሳሰሉትስ እንዴት ነው?

22 የመጨረሻዎቹ ሦስት የመለከት ድምፆች ወዮታ ተብለው ስለ ተጠሩ ከቀደሙት አራት የመለከት ድምፆች የተለዩ ናቸው። (ራእይ 8:13፤ 9:12) ከእነዚህ ሦስት ድምፆች የመጀመሪያዎቹ ሁለት የመለከት ድምፆች አንበጦችና ፈረሰኞች የተካፈሉባቸው ሲሆኑ ሦስተኛው ደግሞ የይሖዋን መንግሥት መወለድ የሚያበስር ነበር። (ራእይ 9:1-21፤ 11:15-19) ወደፊት እንደምንመለከተው የመጨረሻዎቹ ሦስት የይሖዋ ቁጣ ጽዋዎች ከእነዚህ ወዮታዎች ጋር ተመሳሳይነት ቢኖራቸውም ከሦስቱ ወዮታዎች የተለዩ ናቸው። አሁን የይሖዋ ቁጣ ጽዋዎች በመፍሰሳቸው ምክንያት የተከሰተውን አስደናቂ ሁኔታ በጥሞና እንከታተል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.7 የዮሐንስ ክፍል በ1921 በ20 ቋንቋዎችና ከ5 ሚልዮን በሚበልጡ ቅጂዎች የተሰራጨውን የአምላክ በገና የተባለውን መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት የሚረዳ መጽሐፍ አወጣ። ይህም መጽሐፍ ተጨማሪ የተቀቡ መዘምራንን አስገኝቶአል።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]