በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአምላክ ቃል አድራጊዎች ደስታ ያገኛሉ

የአምላክ ቃል አድራጊዎች ደስታ ያገኛሉ

የአምላክ ቃል አድራጊዎች ደስታ ያገኛሉ

“የአምላክ ቃል አድራጊዎች” በተባለው የይሖዋ ምሥክሮች የአውራጃ ስብሰባ መጀመሪያ አካባቢ አንድ ተናጋሪ “ይህ ትልቅ ስብሰባ ይሖዋ እኛን ለተጨማሪ የመንግሥቱ እንቅስቃሴዎች ከሚያዘጋጅባቸው መንገዶች አንዱ እንደሆነ እንገነዘባለን” ብሎ ነበር። አክሎም “ስለ ደስተኛ ቤተሰብ ለመማር፣ ወደ ይሖዋ ድርጅት ተጠግቶ ስለመኖር ማበረታቻ ለማግኘት፣ ለመንግሥቱ አገልግሎት ያለን ቅንዓት እንዳይቀዘቅዝ ለመበረታታትና ንቁዎች ሆኖ መኖር አስፈላጊ ስለመሆኑ ማበረታቻ ለማግኘት ራሳችንን አዘጋጅተናል” በማለት ተናግሯል።

በሚልዮን የሚቆጠሩ የአምላክ ቃል አድራጊዎችና ወዳጆቻቸው ከግንቦት 2000 ማገባደጃ አንስቶ በጣም አስፈላጊ የሆነውን የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ለመቅሰም በዓለም ዙሪያ ወደሚገኙ የተለያዩ መሰብሰቢያ ቦታዎች ጎርፈዋል። ለሦስት ቀናት በቆየው የአውራጃ ስብሰባ ላይ ምን ነገሮች ተምረው ይሆን?

የመጀመሪያው ቀን:- ይሖዋ ያደረጋቸውን ሥራዎች አለመርሳት

የስብሰባው ሊቀ መንበር በመክፈቻው ንግግር ላይ በአውራጃ ስብሰባዎች አማካኝነት ይሖዋን አንድ ሆኖ ማምለክ የሚያስገኘውን በረከት እንዲቀምሱ አድማጮችን ጋበዘ። በስብሰባው ላይ የተገኙ በሙሉ እምነታቸው እንደሚጨምርና ከይሖዋ ጋር የመሠረቱት ዝምድና እንደሚጠናከር አረጋገጠላቸው።

‘ደስተኛው አምላክ’ እያንዳንዳችን ምን ነገር እንደሚያስደስተን ያውቃል። (1 ጢሞቴዎስ 1:​11 NW ) ስለሆነም “የአምላክን ፈቃድ ማድረግ ደስታ ያስገኛል” በሚል ርዕስ የቀረበው ንግግር የይሖዋ ቃል የሆነው መጽሐፍ ቅዱስ ከሁሉ ስለሚሻለው የሕይወት መንገድ እንደሚናገር ጠበቅ አድርጎ ገልጿል። (ዮሐንስ 13:​17) ለረጅም ዓመታት የይሖዋ ምሥክሮች ከነበሩ ሰዎች ጋር የተደረገው ቃለ ምልልስ በምንም ዓይነት ሁኔታዎች ሥር ብንገኝ የአምላክን ፈቃድ ማድረግ ለሕይወታችን የበለጠ ትርጉም እንደሚሰጥ አሳይቷል። “በይሖዋ ጥሩነት ደስ ይበላችሁ” የሚለው ቀጣይ ንግግር ክርስቲያኖች ‘ይሖዋን የሚመስሉ’ እንደመሆናቸው መጠን በሕይወታቸው ‘ጥሩነትን ሁሉ’ ማሳየት እንዳለባቸው የሚያጎላ ነበር። (ኤፌሶን 5:​1, 9 NW ) ጥሩነትን ማሳየት ከሚቻልባቸው ግሩም መንገዶች አንዱ ምሥራቹን መስበክና ደቀ መዛሙርት ማድረግ ነው።​—⁠መዝሙር 145:​7

“የማይታየውን እንደሚታይ አድርጋችሁ ጽኑ” የሚለው ንግግር ጠንካራ እምነት የማይታየውን አምላክ “ለማየት” እንዴት እንደሚረዳ አብራርቷል። ተናጋሪው መንፈሳዊ የሆኑ ሰዎች አምላክ ምን እንደምናስብ የማወቅ ችሎታውን ጨምሮ ሌሎች ባሕርያቱን ማወቅ የሚችሉባቸውን መንገዶች ገልጿል። (ምሳሌ 5:​21) ቃለ ምልልስ የተደረገላቸው ሰዎች ጠንካራ እምነት ለማዳበርና በሕይወታቸው ውስጥ ለመንፈሳዊ ጉዳዮች ቅድሚያ ለመስጠት የወሰዷቸውን እርምጃዎች ተናግረዋል።

የጠዋቱ ፕሮግራም የተጠናቀቀው “ድንቅ ነገሮች የሚያደርገውን ይሖዋን አወድሱ” በሚለው የጭብጡ ቁልፍ ንግግር ነበር። ንግግሩ ስለ ይሖዋ ይበልጥ በተማርን መጠን ድንቅ ስለሆኑት ሥራዎቹ እሱን እንድናወድሰው የሚያደርጉንን ተጨማሪ ምክንያቶችን እያገኘን እንደምንሄድ አድማጮችን አስገንዝቧል። ተናጋሪው እንዲህ ብሎ ነበር:- “ድንቅ የፍጥረት ሥራዎቹን በምናሰላስልበት ጊዜና በአሁኑ ወቅት አምላክ ለእኛ እያደረጋቸው ያሉትን አስደናቂ ነገሮች በምናስብበት ጊዜ ልባችንን ፈንቅሎ የሚወጣው የአድናቆት ስሜት ይሖዋን እንድናወድስ ይገፋፋናል። ለጥንት ሕዝቦቹ ያደረጋቸውን ተዓምራት በምናሰላስልበት ጊዜ እኛም ልናወድሰው እንፈልጋለን። በተጨማሪም ይሖዋ ወደፊት ሊያደርጋቸው ቃል የገባቸውን ነገሮች ስናስብ ለእርሱ ያለንን አድናቆት የምንገልጽባቸውን መንገዶች እንፈልጋለን።”

የከሰዓት በኋላው ፕሮግራም መክፈቻ የሆነው “መልካም ሥራን ለመሥራት አትታክቱ” የሚለው ንግግር በዚህ ዓለም ያሉት አስጨናቂ ሁኔታዎች መጨረሻው መቅረቡን እንደሚያረጋግጡ ተሰብሳቢዎችን በሙሉ አሳስቧል። (2 ጢሞቴዎስ 3:​1) ይሁን እንጂ ተስፋ ባለመቁረጥ “ነፍሳቸውን ሊያድኑ ከሚያምኑቱ” መካከል መሆናችንን ማረጋገጥ እንችላለን።​—⁠ዕብራውያን 10:​39

የቤተሰብ ኑሮን በሚመለከት ምን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምክር ተሰጥቶ ይሆን? “ለአምላክ ቃል ታዘዙ” የሚለው የአውራጃ ስብሰባው የመጀመሪያ ሲምፖዚየም “በትዳር ጓደኛ ምርጫ” በሚል ንግግር ጀመረ። የትዳር ጓደኛ መምረጥ ሰዎች በሕይወታቸው ውስጥ ከሚያደርጓቸው ከባድ ውሳኔዎች መካከል አንዱ ነው። ስለሆነም ክርስቲያኖች ከማግባታቸው በፊት እስኪጎለምሱ ድረስ መጠበቅ እንዲሁም ‘በጌታ ብቻ ማግባት’ ይኖርባቸዋል። (1 ቆሮንቶስ 7:​39) የሲምፖዚየሙ ቀጣይ ክፍል እያንዳንዱ ክርስቲያን ቤተሰብ በመንፈሳዊ ጠንካራ እንዲሆን ይሖዋ እንደሚፈልግ ያብራራ ሲሆን ይህን ማድረግ የሚቻልባቸውን ተግባራዊ መንገዶች ጠቁሟል። የሲምፖዚየሙ የመጨረሻ ክፍል ደግሞ ወላጆች ልጆቻቸው አምላክን እንዲወዱ የሚሰጡት ትምህርት የሚጀምረው እነርሱ ራሳቸው ለአምላክ በሚያሳዩት ፍቅር እንደሆነ አሳስቧል።

“ከወሬና ከሐሜት ተጠበቁ” በሚለው ንግግር ውስጥ የቀረቡት ነጥቦች በጣም አስገራሚ ነገሮች ቢከሰቱም የመስማት ጉጉትን የሚቀሰቅሱ ወሬዎችን በምንሰማበት ጊዜ በቀላሉ ከመታለል ይልቅ በጥበብ መልስ መስጠት እንደሚገባ ትምህርት ሰጥተዋል። ክርስቲያኖች እውነት መሆኑን ስለሚያውቁት ነገር ማለትም ስለ መንግሥቱ ምሥራች ቢናገሩ ጥሩ ነው። ብዙዎች “ያለብንን ‘የሥጋ መውጊያ’ መቋቋም” የሚለውን ቀጣዩን ንግግር አጽናኝና ቀስቃሽ ሆኖ አግኝተውታል። ቀጣይና ፈታኝ ሁኔታዎች ቢያጋጥሙንም ይሖዋ በመንፈስ ቅዱስ፣ በቃሉና በክርስቲያናዊ የወንድማማች ማኅበር አማካኝነት ሊያበረታን እንደሚችል እንዲያስተውሉ ረድቷል። በዚህ ረገድ ሐዋርያው ጳውሎስ ካጋጠመው ሁኔታ ብዙ ማበረታቻ ማግኘት ይቻላል።​—⁠2 ቆሮንቶስ 12:​7-10፤ ፊልጵስዩስ 4:​11, 13

የመጀመሪያው ቀን ስብሰባ “ከይሖዋ ድርጅት ጋር እኩል ተራመዱ” በሚል ንግግር ተደመደመ። የአምላክ ድርጅት እድገት ያደረገባቸውን ሦስት መስኮች:- (1) በመንፈሳዊው ብርሃን ረገድ ከይሖዋ ያገኘነው በየጊዜው እያደገ የሚሄድ ግንዛቤ፣ (2) አምላክ በአደራ የሰጠን አገልግሎት እንዲሁም (3) በድርጅታዊ አሠራር ረገድ የተደረገው ወቅታዊ ማስተካከያ መሆናቸው ተጠቅሷል። ከዚያም ተናጋሪው “በፊታችን ያለውን ጊዜ በታላቅ ጉጉት እንጠባበቃለን” በማለት በትምክህት ተናገረ። አክሎም “በመጀመሪያ የነበረንን ትምክህት እስከ መጨረሻው አጽንተን እንድንይዝ የሚያደርጉን ብዙ ምክንያቶች አሉ” ካለ በኋላ “እነዚህን ምክንያቶች የምንጠራጠርበት ነገር ይኖራልን?” የሚል ጥያቄ አቀረበ። (ዕብራውያን 3:​14) መልሱ ግልጽ ነበር። ከዚያም የአምላክ ወዳጅ መሆን ትችላለህ! የተባለ አዲስ ብሮሹር መውጣቱን አስታወቀ። ዝቅተኛ የትምህርት ደረጃ ወይም ዝቅተኛ የማንበብ ችሎታ ያላቸው ሰዎች ስለ ይሖዋ እንዲያውቁ ለመርዳት የሚያገለግል ጠቃሚ መሣሪያ ነው።

ሁለተኛው ቀን:- ስለ አምላክ ድንቅ ሥራዎች መናገራችሁን ቀጥሉ

የዕለቱ ጥቅስ ከተብራራ በኋላ የአውራጃ ስብሰባው ሁለተኛ ቀን “የአምላክ ቃል አገልጋዮች” በሚል ሲምፖዚየም ቀጠለ። የመጀመሪያው ክፍል ትኩረት ያደረገው ዓለም አቀፉ የስብከት ሥራ በዘመናችን ባስገኘው ስኬት ላይ ነበር። ይሁን እንጂ በሥራው ለመቀጠል የምናሳየው ጽናት የመንግሥቱን መልእክት መስማት በማይፈልጉ በአብዛኞቹ ሰዎች ይፈተናል። ለረዥም ጊዜ ያገለገሉ በርከት ያሉ አስፋፊዎች በአገልግሎት ላይ የሚያጋጥማቸውን ግዴለሽነት ወይም ተቃውሞ ተቋቁመው ደስታቸውን ጠብቀው መቆየት የቻሉት እንዴት እንደሆነ ተናግረዋል። የሲምፖዚየሙ ሁለተኛ ክፍል የይሖዋ ምሥክሮች መደበኛም ሆነ መደበኛ ባልሆነ መንገድ በየስፍራው ሰዎችን አግኝተው ለማነጋገር ጥረት እንዲያደርጉ አሳሰባቸው። የመጨረሻው ክፍል ደግሞ እያንዳንዱ ክርስቲያን አገልግሎቱን ማስፋት የሚችልባቸውን የተለያዩ መንገዶች ገልጿል። ተናጋሪው ይህንን ለማድረግ አንዳንድ አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ማለፍና ራስን መካድ የሚጠይቅበት ቢሆንም እንኳ የአምላክን መንግሥት ከምንም ነገር በላይ ማስቀደም እንደሚገባ ጠበቅ አድርጎ ተናግሯል።​—⁠ማቴዎስ 6:​9-21

ለቁሳዊ ነገሮች ከልክ ያለፈ ግምት በሚሰጥና ለአምላክ አክብሮት በሌለው ዓለም ውስጥ ስለምንኖር “ኑሮዬ ይበቃኛል በማለት ለአምላክ የማደርን ባሕርይ መኮትኮት” የሚለው ንግግር በጣም ወቅታዊ ነበር። ተናጋሪው በ⁠1 ጢሞቴዎስ 6:​6-10, 18, 19 ላይ በመመርኮዝ ለአምላክ የማደር ባሕርይ ክርስቲያኖችን ወደ ስህተትና ወደ ብዙ ሥቃይ ሊመራ ከሚችለው የገንዘብ ፍቅር እንዲርቁ እንደሚረዳቸው ገለጸ። የኑሮ ሁኔታችን ምንም ይሁን ምን ደስታችን የተመካው ከይሖዋ ጋር ባለን ዝምድናና በመንፈሳዊ ደህንነታችን ላይ መሆኑን ጠበቅ አድርጎ ተናግሯል። “አምላክ እንዲያፍርብን ከሚያደርግ ነገር መራቅ” በሚል ርዕስ በቀረበው ንግግር ብዙዎች በእጅጉ ተነክተዋል። ይሖዋ ታማኝ ምሥክሮቹን ፈጽሞ የማይረሳ መሆኑ ጎላ ተደርጎ ተገልጿል። “ትናንትና ዛሬ እስከ ለዘላለምም ያው” የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ የተወው አቻ የማይገኝለት ምሳሌ ብዙዎች የሕይወትን ሩጫ በጽናት እንዲሮጡ ይረዳል።​—⁠ዕብራውያን 13:​8

የይሖዋ ምሥክሮች በሚያደርጓቸው ትላልቅ ስብሰባዎች ላይ ጉልህ ክፍል የሆነው የጥምቀት ንግግር የጠዋቱ ፕሮግራም መደምደሚያ ነበር። ራሳቸውን የወሰኑ አዳዲስ ሰዎች የኢየሱስን ፈለግ በመከተል በውኃ ሲጠመቁ ማየት እንዴት ያስደስታል! (ማቴዎስ 3:​13-17) ሁሉም እዚህ ደረጃ ላይ ከመድረሳቸው በፊት የአምላክ ቃል አድራጊዎች በመሆን ብዙ እርምጃዎችን ወስደዋል። ከዚህም በላይ ሲጠመቁ የተሾሙ የምሥራቹ አገልጋዮች ሆነዋል። የይሖዋን ስም በሚያስቀድስ ሥራ ላይ በመካፈል ላይ እንዳሉ በመገንዘባቸው ከፍተኛ ደስታ አግኝተዋል።​—⁠ምሳሌ 27:​11

“‘መልካምና ክፉ የሆነውን ለመለየት’ ጉልምስና ያስፈልጋል” በሚለው ንግግር ቀጥተኛ ምክር ተሰጥቶ ነበር። ዓለም ትክክልና ስህተት ስለሆነው ነገር የሚያወጣው የአቋም ደረጃ ብዙ ነገር ይጎድለዋል። ስለሆነም ይሖዋ በሚያወጣው የአቋም ደረጃዎች ላይ መደገፍ ያስፈልገናል። (ሮሜ 12:​2) ሁሉም አምላክ ስላ​ወጣቸው የአቋም ደረጃዎች ትክክለኛ የሆነ መረዳት እንዲኖራቸውና ወደ ጉልምስና እንዲያድጉ ጠንክረው መሥራት እንደሚኖርባቸው ማበረታቻ ተሰጥቷቸዋል። ከዚያም የማመዛዘን ችሎታችን በሥራ አማካኝነት “መልካሙንና ክፉውን ለመለየት” እንዲችል ይሠለጥናል።​—⁠ዕብራውያን 5:​11-14

ቀጥሎ የቀረበው “መንፈሳዊነታችሁን ለማሳደግ ጠንክራችሁ ሥሩ” የሚል ሲምፖዚየም ነበር። እውነተኛ ክርስቲያኖች መንፈሳዊነትን ለማዳበርና ጠብቆ ለማቆየት ከሚደረገው ጥረት የተሻለ ምንም ነገር እንደሌለ ይገነዘባሉ። ይህ ደግሞ ጠንክሮ መሥራትን ይኸውም ማንበብ፣ ማጥናትና ማሰላሰል ይጠይቃል። (ማቴዎስ 7:​13, 14፤ ሉቃስ 13:​24) በተጨማሪም መንፈሳውያን ሰዎች ‘ጸሎትና ልመና ሁሉ’ ማቅረባቸውን አያቋርጡም። (ኤፌሶን 6:​18) ጸሎታችን የእምነታችንን ጥልቀትና ለአምላክ ያደርን መሆናችንን፣ የመንፈሳዊነታችንን መጠን እንዲሁም ‘ከሁሉ የተሻለ አድርገን የምንመለከተው ነገር’ ምን እንደሆነ እንደሚያሳይ እንገነዘባለን። (ፊልጵስዩስ 1:​10) አንድ ታዛዥ ልጅ ከአፍቃሪ አባቱ ጋር እንደሚኖረው ዓይነት ዝምድና ከይሖዋ ጋር ሞቅ ያለ ፍቅራዊ ዝምድና ማዳበራችን አስፈላጊ መሆኑ በአጽንዖት ተገልጿል። እውነተኛም እንኳ ቢሆን ሃይማኖት የመያዝ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን አምላክን ‘የማየት ያህል’ ጠንካራ እምነት መገንባት ያስፈልገናል።​—⁠ዕብራውያን 11:​6, 27

መንፈሳዊ እድገት የማድረጉ ጉዳይ “እድገታችሁ ግልጥ ሆኖ ይታይ” በሚለው ንግግር ውስጥ ተጨማሪ ማብራሪያ ተሰጥቶበታል። እድገት ማድረግ የሚቻልባቸው ሦስት መንገዶች:- (1) በእውቀት፣ በማስተዋልና በጥበብ ማደግ፣ (2) የአምላክን መንፈስ ፍሬዎች ማፍራት እንዲሁም (3) በቤተሰብ አባልነታችን ያሉብንን ኃላፊነቶች መወጣት ናቸው።

“በየጊዜው እየጨመረ በሚሄደው የአምላክ የቃል ብርሃን መጓዝ” በሚለው የዕለቱ የመደምደሚያ ንግግር ማብቂያ ላይ የኢሳይያስ ትንቢት​—⁠ለመላው የሰው ዘር የፈነጠቀ ብርሃን! ” የተባለ አዲስ መጽሐፍ በማግኘታቸው በዚያ የተገኙ ተሰብሳቢዎች በጣም ተደስተዋል። የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነውን የኢሳይያስ ትንቢት ምዕራፍ በምዕራፍ ከሚያብራሩት ሁለት መጽሐፎች መካከል ይህ የመጀመሪያው ነው። ተናጋሪው “የኢሳይያስ መጽሐፍ ለእኛ ዘመንም የሚሆን መልእክት አለው” በማለት ተናግሯል። አክሎም “እርግጥ ብዙዎቹ ትንቢቶች በኢሳይያስ ዘመን ፍጻሜያቸውን አግኝተዋል። . . . ይሁን እንጂ ብዙዎቹ የኢሳይያስ ትንቢቶች በዛሬው ጊዜ ፍጻሜያቸውን እያገኙ ሲሆን አንዳንዶቹ የሚፈጸሙት አምላክ ቃል በገባው አዲስ ዓለም ውስጥ ይሆናል” ብሎ ነበር።

ሦስተኛው ቀን:- የቃሉ አድራጊዎች ሁኑ

የአውራጃ ስብሰባው የመጨረሻ ቀን የጀመረው በዕለት ጥቅሱ ላይ ውይይት በማድረግ ነበር። ቀጥሎ “የአምላክን ፈቃድ ለሚያደርጉ ሰዎች ትርጉም ያዘለው የሶፎንያስ ትንቢት” የሚለው ሲምፖዚየም ቀረበ። የዚህ ሲምፖዚየም ሦስት ንግግሮች ይሖዋ በከዳተኛዋ ይሁዳ ዘመን እንዳደረገው ሁሉ በአሁኑ ጊዜም ማስጠንቀቂያውን ለመስማት እምቢተኛ በሆኑ ሁሉ ላይ ታላቅ ጭንቀት እንደሚያመጣባቸው ገልጸዋል። በአምላክ ላይ ኃጢአት ስለሠሩ የመዳኛው መንገድ ጠፍቶት እንደሚደናበር እውር ይሆናሉ። ይሁን እንጂ እውነተኛ ክርስቲያኖች በታማኝነት ይሖዋን መፈለጋቸውን ስለሚቀጥሉ ከአምላክ የቁጣ ቀን ይሰወራሉ። ከዚህም በላይ ደግሞ አሁንም ቢሆን ብዙ በረከቶች ያገኛሉ። የመጽሐፍ ቅዱስን የእውነት ‘ንጹሕ ልሳን’ የመናገር የተባረከ መብት ያገኛሉ። (ሶፎንያስ 3:​9) ተናጋሪው “ስለዚህ በንጹሕ ልሳን መናገር እውነትን በማመንና ለሌሎች በማስተማር ብቻ ተወስኖ የሚቀር ሳይሆን ምግባራችንና ባሕርያችንን ከአምላክ ሕግጋትና መሠረታዊ ሥርዓት ጋር ማስማማትን የሚጨምር ነው” ብሏል።

በአውራጃ ስብሰባው ላይ የተገኙት ሰዎች “ለጊዜያችን የሚሆኑ የማስጠንቀቂያ ምሳሌዎች” የሚለውን ድራማ በጉጉት ሲጠባበቁ ነበር። በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ እስራኤላውያን ይሖዋን በመርሳታቸውና በጣዖት አምላኪ ሴቶች ተታልለው ዝሙት በመፈጸማቸው እንዲሁም በሐሰት አምልኮ በመካፈላቸው በተስፋይቱ ምድር ደፍ ላይ እያሉ እንደሞቱ ድራማው ያመለክታል። ከዋነኞቹ ገጸ ባሕርያት አንዱ የሆነው ያሚን መጀመሪያ ላይ በሞዓባውያን ሴቶች ተማርኮ ለይሖዋ ያደረ ከመሆን አቋሙ ሊሳሳት ምንም አልቀረውም ነበር። የፊንሐስ እምነትና ቆራጥነት ቁልጭ ብሎ እንደታየው ሁሉ አምላካዊ ያልሆነው የዘንበሪ ሐሰተኛና አሳሳች አመለካከትም እንዲሁ ታይቷል። ይሖዋን ከማይወዱ ሰዎች ጋር ወዳጅነት መመሥረት አደገኛ መሆኑ በግልጽ ቀርቧል።

“ሰምታችሁ የምትረሱ አትሁኑ” የሚለው ንግግር በድራማው አማካኝነት የተላለፈውን መልእክት ጎላ አድርጎ ይገልጻል። ለ⁠1 ቆሮንቶስ 10:​1-10 የተሰጠው ማብራሪያ አዲሱን ዓለም ለመውረስ የምንበቃ መሆን አለመሆናችንን ለማረጋገጥ ይሖዋ ታዛዥነታችን እንደሚፈተን ያሳያል። አንዳንዶች አዲሱ ሥርዓት ልንገባ ደፍ ላይ በደረስንበት በአሁኑ ጊዜ ሥጋዊ ፍላጎቶቻቸው መንፈሳዊ ግቦቻቸውን አጣበውባቸዋል። በዚያ የተገኙ ሁሉ ‘ወደ ይሖዋ እረፍት ለመግባት’ ያገኙትን መብት እንዳያጡ ማበረታቻ ተሰጥቷቸዋል።​—⁠ዕብራውያን 4:​1

የሕዝብ ንግግሩ “የአምላክን ድንቅ ሥራዎች በትኩረት መመልከት ያስፈለገበት ምክንያት” የሚል ርዕስ ነበረው። የይሖዋ “ድንቅ ሥራዎች” እርሱ ጥበበኛ እንደሆነና በዙሪያችን ባለው ግዑዝ ፍጥረት ላይ ሥልጣን እንዳለው ግልጽ አድርጎ ያሳያል። (ኢዮብ 37:​14) ኢዮብ ሁሉን ቻይ የሆነው ፈጣሪ ያለውን ኃይል እንዲገነዘብ ይሖዋ አንዳንድ አመራማሪ ጥያቄዎችን ጠየቀው። ወደፊትም ቢሆን ይሖዋ ለታማኝ አገልጋዮቹ ሲል “ድንቅ ሥራዎችን” ያደርጋል። ተናጋሪው “በእርግጥ የይሖዋን ድንቅ ሥራዎች ማለትም ከአሁን በፊት ያደረጋቸውን ባሁኑ ጊዜ በዙሪያችን ባለው ፍጥረት እያደረጋቸው ያሉትን እንዲሁም ወደፊት በቅርብ ጊዜ ውስጥ ሊያደርግልን ቃል የገባልንን ድንቅ ሥራዎች ልብ እንድንል የሚያስገድዱ በጣም ብዙ ምክንያቶች አሉን” በማለት ደምድሟል።

በዚያ ሳምንት የሚጠናው መጠበቂያ ግንብ ከተከለሰ በኋላ የአውራጃ ስብሰባው የመጨረሻ ንግግር ቀረበ። “የአምላክ ቃል አድራጊዎች በመሆን ያገኛችሁትን መብት ከፍ አድርጋችሁ ተመልከቱ” በሚል ርዕስ የቀረበው ቀስቃሽ ንግግር የአምላክ ቃል አድራጊ መሆን መብት እንደሆነ ገልጿል። (ያዕቆብ 1:​22) የአምላክ ቃል አድራጊዎች ለመሆን ያገኙት መብት ልዩ እንደሆነና ይበልጥ በተጠቀምንበት መጠን አድናቆታችንም የዚያኑ ያህል እያደገ እንደሚሄድ ለአድማጮች ማሳሰቢያ ተሰጥቷቸዋል። በስብሰባው ላይ የተገኙ ሁሉ የአምላክ ቃል አድራጊዎች በመሆን የተቻላቸውን እንዲያደርጉ በአውራጃ ስብሰባው ላይ ያገኙትን ጠቃሚ ማነቃቂያ በተግባር እንዲያውሉ ተበረታትተዋል። ከፍተኛ ደስታ የምናገኝበት መንገድ ይህ ብቻ ነው።

[በገጽ 25 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

የአምላክ ወዳጅ መሆን ትችላለህ!

ዓርብ ከሰዓት በኋላ የአምላክ ወዳጅ መሆን ትችላለህ! የተባለ አዲስ ብሮሹር መውጣቱ ተነግሮ ነበር። በብዙ የዓለም ክፍሎች በቀላል መንገድ የተዘጋጀ የመጽሐፍ ቅዱስ መማሪያ ማግኘት ያስፈልግ የነበረ ሲሆን ይህ ብሮሹር ለዚሁ ዓላማ ይውላል። ዝቅተኛ ትምህርት ላላቸው ወይም በደንብ ማንበብ ለማይችሉ ሰዎች ትልቅ በረከት ይሆንላቸዋል።

[በገጽ 25 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

የኢሳይያስ ትንቢት​—⁠ለመላው የሰው ዘር የፈነጠቀ ብርሃን

ተሰብሳቢዎቹ በሁለት ጥራዝ የተዘጋጀውን የኢሳይያስ ትንቢት​—⁠ለመላው የሰው ዘር የፈነጠቀ ብርሃን የተባለውን መጽሐፍ አንደኛ ጥራዝ በማግኘታቸው በጣም ተደስተዋል። መጽሐፉ የኢሳይያስ ትንቢት ለዘመናችን ባለው ተግባራዊ ጠቀሜታ ላይ ያተኩራል።