በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 02

መጽሐፍ ቅዱስ የተስፋ ብርሃን ይፈነጥቃል

መጽሐፍ ቅዱስ የተስፋ ብርሃን ይፈነጥቃል

በዓለም ዙሪያ የሚኖሩ ሰዎች ለሐዘን፣ ለጭንቀት አልፎ ተርፎም ለሥቃይ የሚዳርጉ ችግሮች ያጋጥሟቸዋል። አንተስ እንዲህ እንዲሰማህ የሚያደርግ ችግር ደርሶብህ ያውቃል? ምናልባት የጤና ችግር አጋጥሞህ ወይም የምትወደውን ሰው በሞት አጥተህ ይሆናል። ይህም ‘ወደፊት የተሻለ ጊዜ ይመጣ ይሆን?’ ብለህ እንድትጠይቅ አድርጎህ ሊሆን ይችላል። መጽሐፍ ቅዱስ ለዚህ ጥያቄ የሚሰጠው መልስ ያጽናናሃል።

1. መጽሐፍ ቅዱስ ተስፋ እንዲኖረን የሚረዳን እንዴት ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ ዓለማችን በችግር የተሞላው ለምን እንደሆነ ያብራራል፤ ከዚህም በተጨማሪ እነዚህ ችግሮች ጊዜያዊ እንደሆኑና በቅርቡ እንደሚወገዱ የሚገልጽ ምሥራች ይዟል። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወደፊቱ ጊዜ የያዘው ምሥራች ‘የተሻለ ሕይወትና ተስፋ’ እንዲኖረን ይረዳል። (ኤርምያስ 29:11, 12⁠ን አንብብ።) ይህም በአሁኑ ጊዜ የሚያጋጥሙንን ችግሮች እንድንቋቋም፣ አዎንታዊ አመለካከት እንድንይዝና ዘላቂ ደስታ እንድናገኝ ይረዳናል።

2. መጽሐፍ ቅዱስ ወደፊት ምን ዓይነት ጊዜ እንደሚመጣ ይናገራል?

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወደፊቱ ጊዜ ሲናገር “ከእንግዲህ ወዲህ ሞት አይኖርም፤ ሐዘንም ሆነ ጩኸት እንዲሁም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይኖርም” ይላል። (ራእይ 21:4⁠ን አንብብ።) እንደ ድህነት፣ የፍትሕ መጓደል፣ ሕመምና ሞት ያሉ በዛሬው ጊዜ ሕይወት ተስፋ አስቆራጭ እንዲሆንብን ያደረጉ ችግሮች ይወገዳሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ሰዎች ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለዘላለም በደስታ እንደሚኖሩ ይገልጻል።

3. የመጽሐፍ ቅዱስ ተስፋዎች እንደሚፈጸሙ መተማመን እንድትችል ምን ይረዳሃል?

ብዙ ሰዎች ወደፊት የተሻለ ጊዜ እንደሚመጣ ተስፋ ያደርጋሉ፤ ሆኖም ተስፋቸው እንደሚፈጸም እርግጠኛ መሆን አይችሉም። የመጽሐፍ ቅዱስ ተስፋዎች ግን ከዚህ የተለዩ ናቸው። “ቅዱሳን መጻሕፍትን በሚገባ በመመርመር” እነዚህ ተስፋዎች እንደሚፈጸሙ እርግጠኛ መሆን ትችላለህ። (የሐዋርያት ሥራ 17:11) መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናትህን መቀጠልህ በውስጡ የሚገኙት ተስፋዎች እምነት የሚጣልባቸው መሆን አለመሆናቸውን በራስህ ለመወሰን ይረዳሃል።

ጠለቅ ያለ ጥናት

መጽሐፍ ቅዱስ የወደፊቱን ጊዜ አስመልክቶ ስለሚሰጣቸው አንዳንድ ተስፋዎች እንወያያለን። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘው ተስፋ በዛሬው ጊዜ ሰዎችን እየጠቀመ ያለው እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን።

4. መጽሐፍ ቅዱስ ከችግር ነፃ በሆነ ዓለም ውስጥ ለዘላለም የመኖር ተስፋ እንዳለን ይናገራል

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙትን የሚከተሉትን ተስፋዎች ተመልከት። ከእነዚህ ተስፋዎች መካከል ሲፈጸም ለማየት ይበልጥ የምትጓጓው የትኛውን ነው? ለምንስ?

ከእያንዳንዱ ተስፋ ቀጥሎ የተጠቀሱትን ጥቅሶች አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በእነዚህ ጥቅሶች ላይ የተጠቀሱት ተስፋዎች ለአንተ በግለሰብ ደረጃ እንደሚጠቅሙህ ይሰማሃል? ቤተሰቦችህና ወዳጆችህ እነዚህን ተስፋዎች ቢያውቁ የሚጠቀሙ ይመስልሃል?

የሚከተሉት ነገሮች በሚፈጸሙበት ዓለም ውስጥ ስትኖር ይታይህ፦

ማንም ሰው . . .

ሁሉም ሰው . . .

  • በሞት ያጣቸው የሚወዳቸው ሰዎች ተነስተው ዳግመኛ በምድር ላይ ሲኖሩ ያያል።—ዮሐንስ 5:28, 29

  • ጥሩ ጤንነትና የወጣትነት ጉልበት ይኖረዋል።—ኢዮብ 33:25

  • በጦርነት የተነሳ ችግር ላይ አይወድቅም።—መዝሙር 46:9

  • በሚረብሹ ሐሳቦች ወይም ትዝታዎች ምክንያት ለጭንቀት አይዳረግም።—ኢሳይያስ 65:17

  • ምቹ በሆኑ ሁኔታዎች ሥር ለዘላለም ይኖራል።—መዝሙር 37:29

5. የመጽሐፍ ቅዱስን ተስፋዎች ማወቅ በሕይወታችን ላይ ለውጥ ያመጣል

ብዙ ሰዎች በዙሪያቸው በሚያዩአቸው ችግሮች የተነሳ ለተስፋ መቁረጥ አልፎ ተርፎም ለብስጭት ይዳረጋሉ። አንዳንዶች እነዚህን ሁኔታዎች ለመለወጥ ብዙ ትግል ያደርጋሉ። ወደፊት የተሻለ ጊዜ እንደሚመጣ የሚገልጸው የመጽሐፍ ቅዱስ ተስፋ በዛሬው ጊዜ ሰዎችን እየጠቀመ ያለው እንዴት እንደሆነ ተመልከት። ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ እንደታየው ራፊካን ያሳስባት የነበረው የትኛው ፍትሕ የጎደለው ድርጊት ነው?

  • በዙሪያዋ የምትመለከተው ፍትሕ የጎደለው ድርጊት ባይወገድም መጽሐፍ ቅዱስን ማወቋ የጠቀማት እንዴት ነው?

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘው ተስፋ ችግሮቻችንን በተሳካ ሁኔታ እንድንወጣና በተስፋ መቁረጥ ስሜት እንዳንዋጥ ይረዳናል። ምሳሌ 17:22ን እና ሮም 12:12ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘው ተስፋ በዛሬው ጊዜ የተሻለ ሕይወት እንድትመራ የሚረዳህ ይመስልሃል? እንዲህ የሚሰማህ ለምንድን ነው?

አንዳንዶች እንዲህ ይላሉ፦ “መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጣቸው ተስፋዎች ይፈጸማሉ ብሎ ማመን የማይመስል ነገር ነው።”

  • የመጽሐፍ ቅዱስ ተስፋዎች እንደሚፈጸሙ የሚያሳዩትን ማስረጃዎች ራስህ መመርመርህ ጠቃሚ የሆነው ለምን ይመስልሃል?

ማጠቃለያ

መጽሐፍ ቅዱስ ወደፊት አስደሳች ጊዜ እንደሚመጣ ይናገራል፤ ይህም ተስፋ እንዲኖረን የሚያደርግ ከመሆኑም ሌላ በዛሬው ጊዜ የሚያጋጥሙንን ችግሮች ለመቋቋም ይረዳናል።

ክለሳ

  • ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠውን ተስፋ መስማት የሚያስፈልጋቸው ለምንድን ነው?

  • መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወደፊቱ ጊዜ ምን ተስፋ ይሰጣል?

  • ወደፊት የተሻለ ጊዜ እንደሚመጣ ማወቅህ በዛሬው ጊዜ የሚጠቅምህ እንዴት ነው?

ግብ

ምርምር አድርግ

ተስፋ ችግሮችን ለመቋቋም ኃይል የሚሰጠን እንዴት እንደሆነ አንብብ።

“እውነተኛ ተስፋ ማግኘት የምትችለው ከየት ነው?” (ንቁ! ግንቦት 2004)

ስለ ወደፊቱ ጊዜ የተሰጠው ተስፋ ከከባድ ሕመም ጋር እየታገሉ ያሉ ሰዎችን የሚረዳው እንዴት እንደሆነ አንብብ።

“ከከባድ በሽታ ጋር መኖር—መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው እርዳታ አለ?” (ድረ ገጻችን ላይ የወጣ ርዕስ)

ይህን የሙዚቃ ቪዲዮ ስትመለከት መጽሐፍ ቅዱስ ወደፊት እንደሚመጣ ቃል በገባው ገነት ውስጥ አንተና ቤተሰብህ በደስታ ስትኖሩ በዓይነ ሕሊናህ ለመሳል ሞክር።

ያ ቀን ይታይህ (3:37)

የማኅበራዊ ለውጥ አራማጅ የነበረ አንድ ሰው መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወደፊቱ ጊዜ የሚሰጠውን ተስፋ ሲያውቅ ሕይወቱ እንዴት እንደተለወጠ አንብብ።

“ዓለምን መለወጥ እንዳለብኝ አይሰማኝም” (መጠበቂያ ግንብ ሐምሌ 1, 2013)