በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

ኢየሱስ የአምላክ ልጅ ተብሎ የተጠራው ለምንድን ነው?

ኢየሱስ የአምላክ ልጅ ተብሎ የተጠራው ለምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

 መጽሐፍ ቅዱስ ብዙ ጊዜ ኢየሱስን “የአምላክ ልጅ” በማለት ይጠራዋል። (ዮሐንስ 1:49) “የአምላክ ልጅ” የሚለው አገላለጽ አምላክ ፈጣሪ እንደሆነ ማለትም ኢየሱስን ጨምሮ የሁሉም ፍጥረታት ምንጭ እሱ እንደሆነ የሚጠቁም ነው። (መዝሙር 36:9፤ ራእይ 4:11) መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ እንደ ሰዎች ቃል በቃል ልጅ እንደወለደ አይናገርም።

 መጽሐፍ ቅዱስ መላእክትንም “የእውነተኛው አምላክ ልጆች” በማለት ይጠራቸዋል። (ኢዮብ 1:6) በተጨማሪም የመጀመሪያው ሰው ማለትም አዳም “የአምላክ ልጅ” እንደሆነ ይገልጻል። (ሉቃስ 3:38) ያም ቢሆን ኢየሱስ የአምላክ የመጀመሪያ ፍጥረት በመሆኑና በቀጥታ በአምላክ የተፈጠረው እሱ ብቻ በመሆኑ ኢየሱስ የአምላክ የበኩር ልጅ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይገልጻል።

 ኢየሱስ ምድር ላይ ከመወለዱ በፊት በሰማይ ይኖር ነበር?

 አዎ። ኢየሱስ ሰው ሆኖ ምድር ላይ ከመወለዱ በፊት በሰማይ የሚኖር መንፈሳዊ ፍጡር ነበር። ኢየሱስ ራሱ ‘ከሰማይ እንደመጣ’ ተናግሯል።—ዮሐንስ 6:38፤ 8:23

 አምላክ ኢየሱስን የፈጠረው ሌሎች ነገሮችን ከመፍጠሩ በፊት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስን አስመልክቶ ሲናገር እንዲህ ይላል፦

  •   “እሱ . . . የፍጥረት ሁሉ በኩር ነው።”—ቆላስይስ 1:15

  •   “ከአምላክ ፍጥረት የመጀመሪያ” ነው።—ራእይ 3:14

 “ምንጩ ከጥንት፣ ከረጅም ዘመን በፊት” ስለሆነ መሲሕ የሚናገረው ትንቢት በኢየሱስ ላይ ተፈጽሟል።—ሚክያስ 5:2፤ ማቴዎስ 2:4-6

 ኢየሱስ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት ምን ያደርግ ነበር?

 በሰማይ ከፍተኛ ሥልጣን ነበረው። ኢየሱስ “አባት ሆይ፣ ዓለም ከመመሥረቱ በፊት በጎንህ ሆኜ ክብር እንደነበረኝ ሁሉ አሁንም . . . አክብረኝ” በማለት ያቀረበው ጸሎት ሰማይ ላይ ስለነበረው ሥልጣን የሚገልጽ ነው።—ዮሐንስ 17:5

 አባቱ ሌሎች ነገሮችን ሲፈጥር በሥራው ተካፍሏል። ኢየሱስ “የተዋጣለት ሠራተኛ” በመሆን ከአምላክ ጋር ሠርቷል። (ምሳሌ 8:30) መጽሐፍ ቅዱስ ይህን አስመልክቶ ሲናገር “በሰማያትና በምድር ያሉ ሌሎች ነገሮች በሙሉ . . . የተፈጠሩት በእሱ አማካኝነት ነው” ይላል።—ቆላስይስ 1:16

 አምላክ ሌሎች ነገሮችን የፈጠረው በኢየሱስ አማካኝነት ነው። ከእነዚህ መካከል ጽንፈ ዓለምና መንፈሳዊ ፍጥረታት ይገኙበታል። (ራእይ 5:11) አምላክና ኢየሱስ አብረው የሠሩበት መንገድ በመሐንዲስና በግንበኛ መካከል ካለው ዝምድና ጋር ሊወዳደር ይችላል። መሐንዲሱ ንድፉን ያወጣል፤ ግንበኛው ደግሞ ግንባታውን ይሠራል።

 ቃል ሆኖ አገልግሏል። መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ ሰው ከመሆኑ በፊት ስለነበረው ሕይወት ሲናገር “ቃል” በማለት ይጠራዋል። (ዮሐንስ 1:1) በመሆኑም አምላክ ለሌሎች መንፈሳዊ ፍጥረታት መረጃና መመሪያ ለማስተላለፍ በልጁ ይጠቀም ነበር ማለት ነው።

 ኢየሱስ ምድር ላይ ላሉ ሰዎችም የአምላክ ቃል አቀባይ ሆኖ ሳያገለግል አልቀረም። አምላክ በኤደን ገነት ለአዳምና ለሔዋን መመሪያ የሰጣቸው ኢየሱስን እንደ ቃል አቀባይ ተጠቅሞ ሳይሆን አይቀርም። (ዘፍጥረት 2:16, 17) በተጨማሪም እስራኤላውያንን በምድረ በዳ የመራቸው እንዲሁም ቃሉን እንዲታዘዙ የተነገራቸው መልአክ ኢየሱስ ሊሆን ይችላል።—ዘፀአት 23:20-23 a

a አምላክ የተናገረው ቃል በተባለው መልአክ በኩል ብቻ አይደለም። ለምሳሌ ያህል፣ አምላክ ሕጉን ለጥንቶቹ እስራኤላውያን ለማስተላለፍ አንድያ ልጁን ሳይሆን ሌላ መልአክ ተጠቅሟል።—የሐዋርያት ሥራ 7:53፤ ገላትያ 3:19፤ ዕብራውያን 2:2, 3