በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ጥያቄ 5

በመጽሐፍ ቅዱስ ማመን ምክንያታዊ ነው?

በመጽሐፍ ቅዱስ ማመን ምክንያታዊ ነው?

ስለ አንድ ሰው የተሳሳተ አመለካከት አድሮብህ ያውቃል? ሌሎች ስለዚህ ሰው የተናገሩትን ወይም እንዲህ ብሏል ብለው ያወሩትን ሰምተህ ይሆናል። የምትጠላው ዓይነት ሰው እንደሚሆን ጠብቀህ የነበረ ቢሆንም በደንብ ስታውቀው የተወራበት ነገር ትክክል እንዳልሆነ ትገነዘባለህ። ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በተያያዘም ብዙ ሰዎች ተመሳሳይ ነገር ገጥሟቸዋል።

ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ጥሩ አመለካከት የሌላቸው የተማሩ ሰዎች ጥቂቶች አይደሉም። ለምን እንደሆነ ታውቃለህ? ይህ መጽሐፍ ምክንያታዊና ሳይንሳዊ እንዳልሆነ አሊያም ጨርሶ የተሳሳተ እንደሆነ ተደርጎ ስለሚነገር ወይም በዚህ መንገድ ስለሚጠቀስ ነው። በእርግጥ ሰዎች ስለ መጽሐፍ ቅዱስ የተዛባ አመለካከት እንዲያድርብን ሊያደርጉ ይችላሉ?

ይህን ብሮሹር በምታነብበት ጊዜ መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገረው ሁሉ ከሳይንስ አንጻር ትክክል መሆኑን ስታውቅ አልተገረምክም? ብዙዎች በጣም ይገረማሉ። ከዚህም ሌላ ብዙ ሃይማኖቶች መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል ብለው የሚጠቅሷቸው አንዳንድ ነገሮች መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጨርሶ እንደማይገኙ ሲያውቁ በእጅጉ ተገርመዋል። ለምሳሌ አንዳንዶች ‘መጽሐፍ ቅዱስ፣ አምላክ መላውን ጽንፈ ዓለምና በውስጡ የሚኖሩትን ሕያዋን ነገሮች ሁሉ የፈጠረው የ24 ሰዓት ርዝመት ባላቸው ስድስት ቀናት ውስጥ እንደሆነ ይናገራል’ ይላሉ። እንደ እውነቱ ከሆነ ግን ሳይንቲስቶች ስለ ጽንፈ ዓለምም ሆነ ስለ ምድር ዕድሜ የሚሰጧቸውን የተለያዩ ግምታዊ አስተያየቶች የሚቃረን ነገር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አይገኝም። *

ከዚህም በላይ መጽሐፍ ቅዱስ፣ አምላክ በዚህች ምድር ላይ ሕይወት እንዲገኝ ስላደረገበት መንገድ የሚሰጠው አጭር መግለጫ ለሳይንሳዊ ምርምርና ጽንሰ ሐሳብ ጨርሶ ቦታ የማይሰጥ አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ ሕይወት ያላቸውን ነገሮች በሙሉ እንደፈጠረና ሕይወት ያላቸው ፍጥረታትም “እንደየወገናቸው” እንደተፈጠሩ ይናገራል። (ዘፍጥረት 1:11, 21, 24) እነዚህ መግለጫዎች ከአንዳንድ ሳይንሳዊ ጽንሰ ሐሳቦች ጋር የማይጣጣሙ ሊሆኑ ቢችሉም ከተረጋገጠ ሳይንሳዊ እውነት ጋር አይጋጩም። ጽንሰ ሐሳቦች በየጊዜው እንደሚለዋወጡ የሳይንስ ታሪክ ይመሠክራል፤ እውነታው ግን መቼም አይለወጥም።

ይሁን እንጂ ሃይማኖቶች ተስፋ ስላስቆረጧቸው ብቻ መጽሐፍ ቅዱስን ከመመርመር ወደኋላ የሚሉ ብዙ ሰዎች አሉ። እነዚህ ሰዎች ሃይማኖታዊ ድርጅቶችን ሲመለከቱ በግብዝነትና በምግባረ ብልሹነት የተዘፈቁ ብሎም ጦርነትን የሚናፍቁ እንደሆኑ ይገነዘባሉ። ይሁንና የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያ እንከተላለን የሚሉ አንዳንድ ሰዎች የሚያሳዩትን ምግባር በማየት ብቻ ስለ መጽሐፉ አስተያየት መስጠት ፍትሐዊ ይሆናል? ሰብዓዊነት የሚሰማቸውና ቅን ልብ ያላቸው በርካታ ሳይንቲስቶች፣ ጭፍን ጥላቻ ያላቸው አንዳንድ ጠብ ወዳድ ሰዎች የዝግመተ ለውጥን ጽንሰ ሐሳብ ለዘረኝነት ዓላማቸው መጠቀሚያ ማድረጋቸው በጣም ያበሳጫቸዋል። ታዲያ ይህን ብቻ መሠረት አድርጎ ስለ ዝግመተ ለውጥ ጽንሰ ሐሳብ አስተያየት መስጠት ምክንያታዊ ይሆናል? የጽንሰ ሐሳቡን ይዘት መመርመርና ካለው ማስረጃ ጋር ማነጻጸር የተሻለ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም።

አንተም ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በተያያዘ ተመሳሳይ ነገር እንድታደርግ እናበረታታሃለን። የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት አብዛኞቹ ሃይማኖታዊ ድርጅቶች ከሚያስተምሩት ትምህርት ምን ያህል እንደሚለይ ስታውቅ በጣም ልትገረም ትችላለህ። መጽሐፍ ቅዱስ ጦርነትና የጎሣ ግጭት ከማስፋፋት ይልቅ የአምላክ አገልጋዮች ከጦርነትም ሆነ ለውጊያ ምክንያት ከሆነው ከጥላቻ መራቅ እንዳለባቸው ያስተምራል። (ኢሳይያስ 2:2-4፤ ማቴዎስ 5:43, 44፤ 26:52) በተጨማሪም ጽንፈኞች እንድንሆንና በማስረጃ ያልተደገፈ ጭፍን እምነት እንዲኖረን ሳይሆን ለትክክለኛ እምነት፣ ማስረጃ የግድ አስፈላጊ እንደሆነ እንዲሁም አምላክን ለማገልገል የማሰብ ችሎታን መጠቀም ወሳኝ እንደሆነ ያስተምራል። (ሮም 12:1፤ ዕብራውያን 11:1) ከዚህም በላይ ለማወቅ ያለንን ጉጉት ከማዳፈን ይልቅ ሰዎች ለሚፈጠሩባቸው ከባድና ትኩረት የሚስቡ ጥያቄዎች መልስ ለማግኘት እንድንጥር ያበረታታል።

ለምሳሌ ‘በእርግጥ አምላክ ካለ ክፋት እንዲኖር የፈቀደው ለምንድን ነው’ ብለህ አስበህ ታውቃለህ? መጽሐፍ ቅዱስ ለዚህም ሆነ ለሌሎች በርካታ ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ ይሰጣል። * እውነቱን ለማወቅ በምታደርገው ጥረት እንድትቀጥል እናበረታታሃለን። አርኪ፣ አስደሳችና ምክንያታዊ የሆኑ አልፎ ተርፎም በአሳማኝ ማስረጃዎች ላይ የተመሠረቱ መልሶች ማግኘት ትችላለህ። ይህ ደግሞ እንዲሁ በአጋጣሚ የሆነ ነገር አይደለም።

^ አን.5 ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት ሕይወት የተገኘው በፍጥረት ነው? የተባለውን በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀ ብሮሹር ተመልከት።