በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በቅርቡ ስለሚፈጸሙ ነገሮች የተነገሩ ትንቢቶች

በቅርቡ ስለሚፈጸሙ ነገሮች የተነገሩ ትንቢቶች

በቅርቡ ስለሚፈጸሙ ነገሮች የተነገሩ ትንቢቶች

ሐዋርያው ጴጥሮስ፣ የሰው ልጆችንና የምድርን የወደፊት ሁኔታ አስመልክቶ እንዲህ በማለት ጽፏል፦ “ጽድቅ የሚኖርበትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር [በአምላክ የተስፋ ቃል] መሠረት እንጠባበቃለን።” (2 ጴጥሮስ 3:13) ‘ስለ አዲስ ሰማያትና አዲስ ምድር’ ለመጀመሪያ ጊዜ የተናገረው ነቢዩ ኢሳይያስ ነው። (ኢሳይያስ 65:17፤ 66:22) ጴጥሮስ ይህንን ትንቢት ጠቅሶ መናገሩ ትንቢቱ በእሱ ዘመንም ሙሉ በሙሉ ፍጻሜውን እንዳላገኘ ያሳያል።

ቆየት ብሎ በ96 ከክርስቶስ ልደት በኋላ ገደማ፣ ሐዋርያው ዮሐንስ ባየው ራእይ ላይ “አዲስ ምድር” የአምላክ መንግሥት ከሚያመጣቸው በረከቶች ጋር ተያይዞ ተጠቅሷል። (ራእይ 21:1-4) ኢየሱስም ሆነ ሐዋርያው ጳውሎስ፣ የአምላክ መንግሥት ከመምጣቱ በፊት በዓለም ላይ ስለሚከሰቱት ሁኔታዎች የተናገሯቸው ትንቢቶች ፍጻሜያቸውን በማግኘት ላይ ናቸው። በመሆኑም ይህ መንግሥት በቅርቡ አዲስ ዓለም እንደሚያመጣ መጠበቅ እንችላለን። የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው የኢሳይያስ መጽሐፍ ይህ አዲስ ዓለም ምን እንደሚመስል ይነግረናል።

በአዲስ ዓለም ውስጥ የሚገኙ በረከቶች

ዓለም አቀፍ ሰላምና የአምልኮ አንድነት። “ሰይፋቸውን ቀጥቅጠው ማረሻ ጦራቸውንም ጭድ ያደርጋሉ። ሕዝብ በሕዝብ ላይ ሰይፍ አያነሣም፤ ጦርነትንም ከእንግዲህ አይማሩም።”—ኢሳይያስ 2:2-4

በሰዎችና በእንስሳት መካከል ሰላም ይሰፍናል። “ተኵላ ከበግ ጠቦት ጋር ይኖራል፤ ነብርም ከፍየል ግልገል ጋር ይተኛል፤ ጥጃ፣ የአንበሳ ደቦልና የሰባ ከብት በአንድነት ይሰማራሉ፤ ትንሽ ልጅም ይመራቸዋል። ላምና ድብ በአንድነት ይሰማራሉ፤ ልጆቻቸውም አብረው ይተኛሉ፤ አንበሳም እንደ በሬ ገለባ ይበላል። . . . በተቀደሰው ተራራዬ ሁሉ ላይ ጕዳት ወይም ጥፋት አያደርሱም፤ ውሃ ባሕርን እንደሚሸፍን፣ ምድር ሁሉ እግዚአብሔርን በማወቅ ትሞላለችና።”—ኢሳይያስ 11:6-9

የተትረፈረፈ ምግብ ይኖራል። “የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር በዚህ ተራራ ላይ፣ ለሕዝብ ሁሉ ታላቅ የምግብ ግብዣ፣ የበሰለ የወይን ጠጅ ድግስ፣ ማለፊያ ጮማና ምርጥ የወይን ጠጅ ያዘጋጃል።”—ኢሳይያስ 25:6

ሞት አይኖርም። “[አምላክ] ሞትንም ለዘላለም ይውጣል። ጌታ እግዚአብሔር ከፊት ሁሉ እንባን ያብሳል፤ የሕዝቡንም ውርደት ከምድር ሁሉ ያስወግዳል፤ እግዚአብሔር ተናግሮአልና።”—ኢሳይያስ 25:8

የሞቱ ሰዎች ይነሳሉ። “ሙታንህ ሕያዋን ይሆናሉ፤ በድናቸውም ይነሣል። እናንት በዐፈር ውስጥ የምትኖሩ፣ ተነሡ፤ በደስታም ዘምሩ። . . . ምድር ሙታንን ትወልዳለች።”—ኢሳይያስ 26:19

መሲሑ በጽድቅ ይፈርዳል። “ዐይኑ እንዳየ አይፈርድም፤ ጆሮውም እንደ ሰማ አይበይንም። ነገር ግን ለድኾች በጽድቅ ይፈርዳል፤ ለምድር ምስኪኖችም ፍትሕን ይበይናል።”—ኢሳይያስ 11:3, 4

ማየትና መስማት የተሳናቸው ሰዎች ይፈወሳሉ። “በዚያን ጊዜም የዕውር ዐይኖች ይገለጣሉ፤ የደንቈሮም ጆሮዎች ይከፈታሉ።”—ኢሳይያስ 35:5

ጠፍ የሆነው ምድር ፍሬያማ ይሆናል። “ምድረ በዳውና ደረቁ ምድር ደስ ይላቸዋል፤ በረሓው ሐሤት ያደርጋል፤ ይፈካል፤ እንደ አደይም ያብባል። በደስታና በዝማሬ ሐሤት ያደርጋል።”—ኢሳይያስ 35:1, 2

አዲስ ምድር። “እኔ፣ አዲስ ሰማያትንና [አዲስ ሰማያዊ መስተዳደርና] አዲስ ምድርን [ጻድቅ የሆነ አዲስ ኅብረተሰብ] እፈጥራለሁ፤ ያለፉት ነገሮች አይታሰቡም፤ አይታወሱም። ነገር ግን በምፈጥረው፣ ደስ ይበላችሁ፤ ለዘላለም ሐሤት አድርጉ። . . . [አምላክ ቃል በገባው አዲስ ዓለም ውስጥ የሚኖሩ] ሰዎች ቤት ይሠራሉ፤ በውስጡም ይኖራሉ፤ ወይንን ይተክላሉ፤ ፍሬውንም ይበላሉ። ከእንግዲህ ለሌሎች መኖሪያ ቤት አይሠሩም፤ ወይም ሌላው እንዲበላው አይተክሉም፤ የሕዝቤ ዕድሜ፣ እንደ ዛፍ ዕድሜ ይረዝማል፤ እኔ የመረጥኋቸው፣ በእጃቸው ሥራ ለረጅም ዘመን ደስ ይላቸዋል። ድካማቸው በከንቱ አይቀርም፤ ዕድለ ቢስ ልጆችም አይወልዱም፤ እነርሱና ዘራቸው፣ እግዚአብሔር የባረከው ሕዝብ ይሆናሉ። ገና ሳይጣሩ እመልስላቸዋለሁ፤ ተናግረው ሳይጨርሱ እሰማለሁ።” “‘እኔ የምሠራቸው አዲስ ሰማያትና አዲስ ምድር በፊቴ ጸንተው እንደሚኖሩ፣ የእናንተና የዘራችሁ ስም እንደዚሁ ጸንቶ ይኖራል’ ይላል እግዚአብሔር።”—ኢሳይያስ 65:17-25፤ 66:22

ታላቅ ተስፋ የያዘ ትንቢት

ወደፊት ስለሚመጡት በረከቶች የሚናገረው የኢሳይያስ መጽሐፍ ብቻ አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስ፣ አምላክ በክርስቶስ በሚመራው መንግሥቱ አማካኝነት ስለሚፈጽማቸው አስደናቂ ነገሮች በሚገልጹ ትንቢቶች የተሞላ ነው። * እንዲህ በመሰለው ገነት ውስጥ ለመኖር ትፈልጋለህ? የምትፈልግ ከሆነ አምላክ ስለ ወደፊቱ ጊዜ ያለውን መልካም ዓላማ በተመለከተ ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምን እንደሆነ ለምን አትመረምርም? ከዚህ በረከት ተካፋይ መሆን የምትችለው እንዴት እንደሆነ እንድትማር እናበረታታሃለን። የይሖዋ ምሥክሮች አንተን ለመርዳት ፈቃደኞች ናቸው።

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

^ አን.15 ስለ አምላክ መንግሥትና ስለሚያከናውናቸው ነገሮች የበለጠ ለማወቅ ከፈለግህ ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? የተባለውን መጽሐፍ ከገጽ 76-85 ተመልከት።

[በገጽ 8 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሰዎች እርስ በርሳቸውም ሆነ ከእንስሳት ጋር በሰላም ይኖራሉ

[በገጽ 9 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሙታን እንደገና ሕያው ይሆናሉ

[በገጽ 10 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

መላዋ ምድር ገነት ትሆናለች