ክፍል 5
የመንግሥቱ የትምህርት መርሐ ግብር—የንጉሡን አገልጋዮች ማሠልጠን
መድረክ ላይ ያለውን ተናጋሪ በሚያበረታታ መልኩ ፈገግ ብለህ እያየኸው ነው። ተናጋሪው፣ በጉባኤህ ያለ ወጣት ወንድም ሲሆን በትልቅ ስብሰባ ላይ ንግግር ሲያቀርብ የመጀመሪያ ጊዜው ነው። ንግግሩን እያዳመጥክ እያለ የአምላክ ሕዝቦች ስለሚያገኙት ሥልጠና በማሰብ ትገረማለህ። ይህ ወጣት ለመጀመሪያ ጊዜ ክፍል ሲያቀርብ የነበረውን ሁኔታ ታስታውሳለህ፤ ወንድም ከዚያ ወዲህ ያደረገው እድገት አስገራሚ ነው! በአቅኚነት አገልግሎት ትምህርት ቤት ሥልጠና ካገኘ በኋላ ጥሩ እድገት አድርጓል። በቅርቡ ደግሞ እሱና ባለቤቱ በመንግሥቱ ወንጌላውያን ትምህርት ቤት ተካፍለዋል። ወንድም ግሩም አድርጎ ያቀረበውን ንግግር ሲጨርስ አድናቆትህን ለመግለጽ እያጨበጨብክ የአምላክ ሕዝቦች በሙሉ ስለሚያገኙት ሥልጠና ማሰብ ትጀምራለህ።
መጽሐፍ ቅዱስ የአምላክ ሕዝቦች ሁሉ “ከይሖዋ የተማሩ” የሚሆኑበት ጊዜ እንደሚመጣ አስቀድሞ ተናግሯል። (ኢሳ. 54:13) የምንኖረው ይህ ትንቢት እየተፈጸመ ባለበት ጊዜ ውስጥ ነው። ከጽሑፎቻችን በተጨማሪ በጉባኤ እና በትላልቅ ስብሰባዎች አማካኝነት ትምህርት ይሰጠናል፤ እንዲሁም በይሖዋ ድርጅት ውስጥ እኛን ለተለያዩ ሥራዎች ለማሠልጠን ተብለው ከተዘጋጁ ትምህርት ቤቶች ጥቅም እናገኛለን። ይህ ሁሉ ሥልጠና የአምላክ መንግሥት በዛሬው ጊዜ እየገዛ መሆኑን የሚያረጋግጠው እንዴት እንደሆነ በዚህ ክፍል ላይ እንመረምራለን።