በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አንድን ጥንታዊ ጥቅልል ማንበብ ተቻለ

አንድን ጥንታዊ ጥቅልል ማንበብ ተቻለ

በ1970 በኤንገዲ የተገኘውን የተቃጠለ ጥቅልል ማንበብ አልተቻለም ነበር። በቅርቡ ግን የተራቀቀ ምስል ማንሻ መሣሪያ በመጠቀም፣ ጥቅልሉ የአምላክን የግል ስም ጨምሮ የዘሌዋውያንን መጽሐፍ የተወሰነ ክፍል እንደያዘ ማወቅ ተችሏል

በ1970 የአርኪኦሎጂ ባለሙያዎች፣ እስራኤል ውስጥ በሙት ባሕር ምዕራባዊ ዳርቻ አቅራቢያ በምትገኘው በኤንገዲ አንድ የተቃጠለ ጥቅልል ቆፍረው አወጡ። ጥቅልሉን ያገኙት ተቀብሮ የነበረ አንድ ምኩራብ እየቆፈሩ በነበሩበት ጊዜ ነው፤ በስድስተኛው መቶ ዘመን ዓ.ም. አካባቢ መንደሩ በጠፋበት ወቅት ምኩራቡ ተቃጥሎ ነበር። ጥቅልሉ በጣም ከመጎዳቱ የተነሳ በላዩ የሰፈረውን ጽሑፍ ማንበብ አይቻልም ነበር፤ ጥቅልሉን ለመተርተር ቢሞከር እንኳ ከጥቅም ውጭ ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ የተራቀቀ ምስል ማንሻ መሣሪያ (3-D ስካነር) በመጠቀም፣ በጥቅልሉ ውስጥ ያሉትን ነገሮች ምስል ማንሳት ተቻለ። ከዚያም ዘመናዊ በሆነ የኮምፒውተር ፕሮግራም እገዛ፣ በጥቅልሉ ላይ የተጻፈው ነገር ሊነበብ ችሏል።

ታዲያ ምን ተገኘ? ጥቅልሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ የያዘ መሆኑን ማወቅ ተችሏል። ከቃጠሎው የተረፈው የጥቅልሉ ክፍል በዘሌዋውያን መጽሐፍ የመጀመሪያ ምዕራፍ ላይ የሚገኙ ጥቅሶችን ይዟል። በእነዚህ ጥቅሶች ላይ የአምላክን የግል ስም የሚወክሉት አራት የዕብራይስጥ ፊደላት ይገኛሉ። ጥቅልሉ የተዘጋጀው ከ50 ዓ.ም. እስከ 400 ዓ.ም. ባለው ጊዜ መካከል ሳይሆን አይቀርም፤ በመሆኑም ከሙት ባሕር (ኩምራን) ጥቅልሎች ቀጥሎ በጣም ጥንታዊው የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት ቅጂ ነው ማለት ይቻላል። ጊል ጾሃር፣ ዘ ጀሩሳሌም ፖስት በተባለው ጋዜጣ ላይ እንዲህ ብለዋል፦ “በኤንገዲ የተገኘው የዘሌዋውያን መጽሐፍ ቁራጭ ይዘት መነበብ እስከቻለበት ጊዜ ድረስ፣ በሁለተኛው ቤተ መቅደስ ዘመን በነበሩት 2,000 ዓመታት የሆናቸው የሙት ባሕር ጥቅልሎችና በ10ኛው መቶ ዘመን ዓ.ም. በተጻፈው የመካከለኛው ዘመን የአሌፖ ኮዴክስ መካከል የአንድ ሺህ ዓመት ልዩነት ነበረ።” ምሁራኑ እንደሚሉት ከሆነ በዚህ ጥቅልል ላይ የሚገኘው ሐሳብ፣ የቶራ ጽሑፍ “ከአንድ ሺህ ዓመታት ለሚበልጥ ጊዜ በትክክል ተጠብቆ እንደቆየና የገልባጮች ስህተት በጽሑፉ ላይ ለውጥ እንዳላመጣ” ያረጋግጣል።