በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ወደ አምላክ ቅረብ

‘እኔ አልረሳሽም’

‘እኔ አልረሳሽም’

ይሖዋ በእርግጥ ስለ ሕዝቡ ያስባል? ከሆነስ ምን ያህል በጥልቅ ያስብልናል? የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ ማወቅ የምንችልበት ብቸኛው መንገድ አምላክ የተናገረውን መመልከት ነው። ይሖዋ ለእኛ ያለውን ስሜት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በግልጽ ነግሮናል። በ⁠ኢሳይያስ 49:15 ላይ ያለውን ሐሳብ እስቲ እንመልከት።

ይሖዋ ለሕዝቡ ያለውን ጥልቅ አሳቢነት ለመግለጽ ልናስበው ከምንችለው ሁሉ ይበልጥ ልብ የሚነካ ምሳሌ ተጠቅሟል። ይሖዋ በኢሳይያስ መጽሐፍ ላይ ተመዝግቦ የምናገኘውን ይህን ምሳሌ የጀመረው የሚከተሉትን ስሜት የሚኮረኩሩ ጥያቄዎች በመጠየቅ ነበር፦ “እናት የምታጠባውን ልጇን ልትረሳ ትችላለችን? ለወለደችውስ ልጅ አትራራለትምን?” መጀመሪያ ላይ የጥያቄዎቹ መልስ ግልጽ ይመስል ይሆናል። አንዲት የምታጠባ እናት እንዴት ልጇን ልትረሳ ትችላለች? ልጇ ቀን ከሌት የእሷ እንክብካቤ ያሻዋል፤ ደግሞም ትኩረቷን ማግኘት ሲፈልግ ያለቅሳል! ይሖዋ ያነሳው ጥያቄ ግን ከዚህ ያለፈ ትርጉም ያዘለ ነው።

አንዲት እናት ልጇን የምታጠባውና የሚያስፈልገውን ሁሉ የምታሟላለት ለምንድን ነው? ማልቀሱን እንዲያቆም ለማድረግ ብቻ ነው? አይደለም። አንዲት እናት “ከማኅፀንዋ ለተወለደው ልጅ” (የ1954 ትርጉም) ተፈጥሯዊ ‘ርኅራኄ’ ታሳያለች። እዚህ ላይ ‘መራራት’ ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ግስ ‘ምሕረት ማድረግ’ ተብሎም ሊፈታ ይችላል። (ዘፀአት 33:19፤ ኢሳይያስ 54:10) ይህ የዕብራይስጥ ቃል ረዳት ለሌላቸው ወይም ደካማ ለሆኑ ሰዎች ከአንጀት የመነጨ ርኅራኄ ማሳየትን ያመለክታል። አንዲት እናት ለምታጠባው ልጇ የምታሳየው ርኅራኄ ልናስበው ከምንችለው የላቀ ነው።

የሚያሳዝነው ግን ለሚያጠቡት ሕፃን የሚራሩት ሁሉም እናቶች አይደሉም። ይሖዋ “ምናልባት እርሷ [የምታጠባ እናት] ትረሳ ይሆናል” ብሏል። የምንኖረው “ታማኝ ያልሆኑ [እና] ተፈጥሯዊ ፍቅር የሌላቸው” ሰዎች በበዙበት ዓለም ውስጥ ነው። (2 ጢሞቴዎስ 3:1-5) አንዳንድ ጊዜ አራስ ልጃቸውን ችላ ስለሚሉ፣ ስለሚያጎሳቁሉ ወይም ስለሚጥሉ እናቶች እንሰማለን። አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ የማመሳከሪያ ጽሑፍ ኢሳይያስ 49:15⁠ን በተመለከተ እንዲህ ይላል፦ “እናቶች ኃጢአተኞች በመሆናቸው አንዳንድ ጊዜ የራስ ወዳድነት ስሜታቸው ሊያይልና ልጃቸውን ፍቅር እንዲነፍጉት ሊያደርጋቸው ይችላል። በሰዎች ዘንድ ታላቅ የሚባለው ይህ ፍቅር እንኳ ሊቀዘቅዝ ይችላል።”

ይሖዋ፣ ለእስራኤል ብሔር “እኔ ግን አልረሳሽም” የሚል ማረጋገጫ ሰጥቷቸው ነበር፤ ይህ ለእኛም ይሠራል። ይሖዋ በ⁠ኢሳይያስ 49:15 ላይ እንዲህ ዓይነት ጥያቄ ያነሳበትን ዓላማ አሁን መረዳት እንችላለን። እዚህ ላይ ይሖዋ ራሱን ከምታጠባ እናት ጋር እያመሳሰለ ሳይሆን በሁለቱ መካከል ያለውን ጉልህ ልዩነት እየገለጸ ነው። የእነሱን እርዳታ ለሚሹ አራስ ልጆቻቸው ርኅራኄ ከማያሳዩ ፍጽምና የጎደላቸው እናቶች በተቃራኒ ይሖዋ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው አገልጋዮቹ ርኅራኄ ማሳየትን መቼም ቢሆን አይረሳም። ከላይ የተጠቀሰው የማመሳከሪያ ጽሑፍ ስለ ኢሳይያስ 49:15 ሲናገር “ይህ፣ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ከሚገኙ የአምላክን ፍቅር የሚያሳዩ እጅግ ግሩም አገላለጾች አንዱ ነው” ማለቱ የተገባ ነው።

“አምላካችን ከአንጀት የመነጨ ርኅራኄ” እንደሚያሳይ ማወቁ የሚያጽናና አይደለም? (ሉቃስ 1:78) ወደ ይሖዋ ይበልጥ መቅረብ የምትችለው እንዴት እንደሆነ ለምን አትማርም? ይህ አፍቃሪ አምላክ ለአገልጋዮቹ “ፈጽሞ አልተውህም፣ በምንም ዓይነት አልጥልህም” የሚል ማረጋገጫ ሰጥቷቸዋል።​—ዕብራውያን 13:5

በየካቲት ወር የሚነበብ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል፦

ኢሳይያስ 43 እስከ 62