አምላክ ማን ነው?
ከአምላክ ቃል ተማር
አምላክ ማን ነው?
ይህ ርዕሰ ትምህርት በአእምሮህ ሊመላለሱ የሚችሉ ጥያቄዎችን የሚያነሳ ሲሆን መልሶቹን ከመጽሐፍ ቅዱስህ ውስጥ የት ቦታ ላይ ማግኘት እንደምትችልም ይጠቁምሃል። የይሖዋ ምሥክሮች ለጥያቄዎቹ በተሰጡት መልሶች ላይ ከአንተ ጋር ቢወያዩ ደስ ይላቸዋል።
1. አምላክ ማን ነው?
እውነተኛው አምላክ የሁሉም ነገር ፈጣሪ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ አምላክን “የዘላለም ንጉሥ” ብሎ የሚጠራው ሲሆን “የዘላለም” የሚለው ቃል መጀመሪያም ሆነ መጨረሻ እንደሌለው የሚያመለክት ነው። (ራእይ 15:3) አምላክ የሕይወት ምንጭ ስለሆነ ማምለክ የሚኖርብን እሱን ብቻ ነው።—ራእይ 4:11ን አንብብ።
2. ፈጣሪያችን ምን ዓይነት አምላክ ነው?
አምላክ መንፈሳዊ አካል ያለው በመሆኑ ማንም ሰው አይቶት አያውቅም፤ ይህ ደግሞ መንፈሳዊ አካል በምድር ላይ ያሉ ፍጥረታት ካላቸው አካል እጅግ የላቀ መሆኑን ያሳየናል። (ዮሐንስ 1:18፤ 4:24) ሆኖም የአምላክን ባሕርያት ከሠራቸው ነገሮች በግልጽ መመልከት ይቻላል። ለምሳሌ ያህል፣ ፍራፍሬዎችና አበቦች የረቀቀ ንድፍ እንዳላቸውና ዓይነታቸው በጣም ብዙ እንደሆነ ስንመለከት አምላክ ምን ያህል አፍቃሪና ጥበበኛ እንደሆነ እንረዳለን። የጽንፈ ዓለም ስፋት ደግሞ የአምላክ ኃይል ምን ያህል ታላቅ እንደሆነ ለመረዳት ያስችለናል።—ሮም 1:20ን አንብብ።
መጽሐፍ ቅዱስ ስለ አምላክ ባሕርያት ይበልጥ እንድናውቅ ያስችለናል። ለምሳሌ አምላክ ምን እንደሚወድና ምን እንደሚጠላ እንዲሁም ሰዎችን እንዴት እንደሚይዝና የተለያዩ ሁኔታዎች ሲያጋጥሙት ምን ዓይነት ምላሽ እንደሚሰጥ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል።—መዝሙር 103:7-10ን አንብብ።
3. አምላክ ስም አለው?
ኢየሱስ “በሰማያት የምትኖር አባታችን፣ ስምህ ይቀደስ” ብሏል። (ማቴዎስ 6:9) አምላክ ብዙ የማዕረግ ስሞች ቢኖሩትም የግል ስሙ ግን አንድ ብቻ ነው። የዚህ ስም አነባበብ ከቋንቋ ቋንቋ ይለያያል። ለምሳሌ በአማርኛ “ይሖዋ” ወይም “ያህዌ” ተብሎ ይጠራል።—ዘፀአት 6:3ን በ1879 ትርጉም አንብብ።
የአምላክ ስም ከብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች ውስጥ እንዲወጣ ተደርጎ ጌታ ወይም አምላክ በሚሉት የማዕረግ ስሞች ተተክቷል። ይሁንና መጽሐፍ ቅዱስ መጀመሪያ በተጻፈባቸው ቋንቋዎች የአምላክ ስም 7,000 ለሚያህሉ ጊዜያት ተጠቅሷል። ኢየሱስ የአምላክን ቃል ለሰዎች ሲያስተምር በዚህ ስም በመጠቀም የአምላክ ስም እንዲታወቅ አድርጓል። እንዲህ በማድረግ ሰዎች አምላክን እንዲያውቁ ረድቷቸዋል።—ዮሐንስ 17:26ን አንብብ።
4. ይሖዋ ስለ እኛ ያስባል?
አምላክ ጸሎታችንን በግለሰብ ደረጃ መስማቱ ለእኛ ያለውን አሳቢነት ያሳያል። (መዝሙር 65:2) በአሁኑ ጊዜ ሥቃይና መከራ ስለበዛ አምላክ ስለ እኛ አያስብም ማለት ነው? አንዳንድ ሰዎች አምላክ እኛን ለመፈተን ሲል ሥቃይ እንዲደርስብን ያደርጋል ይላሉ፤ ይሁንና ይህ ፈጽሞ ከእውነት የራቀ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ “ክፋትን ማድረግ ከእግዚአብሔር ዘንድ . . . ይራቅ” በማለት ይናገራል።—ኢዮብ 34:10፤ ያዕቆብ 1:13ን አንብብ።
አምላክ ለሰው ልጆች ነፃ ምርጫ የማድረግ መብት በመስጠት አክብሯቸዋል። ታዲያ በዚህ ነፃነታችን ተጠቅመን አምላክን ለማገልገል መምረጥ በመቻላችን አመስጋኝ ልንሆን አይገባም? (ኢያሱ 24:15) መከራና ሥቃይ እንዲህ ሊበዛ የቻለው ብዙዎች በሌሎች ላይ መጥፎ ነገር ለማድረግ ስለመረጡ ነው። ይሖዋ እንዲህ ዓይነቱን ግፍ ሲመለከት ልቡ ያዝናል።—ዘፍጥረት 6:5, 6ን አንብብ።
በቅርቡ ይሖዋ በኢየሱስ አማካኝነት መከራንም ሆነ ለመከራ መንስኤ የሆኑትን በሙሉ ጠራርጎ ያጠፋል። ይሖዋ ለጊዜው መከራና ሥቃይ እንዲደርስብን የፈቀደበት በቂ ምክንያት አለው። የዚህ ዓምድ ቀጣይ ክፍል አምላክ መከራና ሥቃይ እንዲኖር የፈቀደው ለምን እንደሆነ ያብራራል።—ኢሳይያስ 11:4ን አንብብ።
5. አምላክ ምን እንድናደርግ ይፈልጋል?
ይሖዋ የፈጠረን እሱን ማወቅና መውደድ እንድንችል አድርጎ ነው። ስለ እሱ እውነቱን እንድናውቅ ይፈልጋል። (1 ጢሞቴዎስ 2:4) መጽሐፍ ቅዱስን የምናጠና ከሆነ አምላክን የጓደኛ ያህል ልንቀርበው እንችላለን።—ምሳሌ 2:4, 5ን አንብብ።
ሕይወት የሰጠን ይሖዋ በመሆኑ ከማንም በላይ እሱን መውደድ ይኖርብናል። በጸሎት አማካኝነት ከአምላክ ጋር በመነጋገርና እንድናደርግ የሚፈልግብንን ነገር በመፈጸም እንደምንወደው ማሳየት እንችላለን። (ምሳሌ 15:8) በተጨማሪም ይሖዋ ሌሎች ሰዎችን በፍቅር እንድንይዝ ይፈልጋል።—ማርቆስ 12:29, 30ን እና 1 ዮሐንስ 5:3ን አንብብ።
ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀውን ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 1 ተመልከት።
[በገጽ 17 ላይ የሚገኝ ፎቶ]
አምላክ ለጊዜው መከራና ሥቃይ እንዲኖር የፈቀደበት አጥጋቢ ምክንያት ሊኖር ይችላል?