ሁለተኛ ዜና መዋዕል 4:1-22

  • መሠዊያው፣ ባሕሩና ገንዳዎቹ (1-6)

  • መቅረዞቹ፣ ጠረጴዛዎቹና ግቢዎቹ (7-11ሀ)

  • የቤተ መቅደሱ ዕቃዎች ተሠርተው ተጠናቀቁ (11ለ-22)

4  ከዚያም ርዝመቱ 20 ክንድ፣ ወርዱ 20 ክንድ፣ ከፍታውም 10 ክንድ የሆነ የመዳብ መሠዊያ ሠራ።+ 2  ባሕሩን*+ በቀለጠ ብረት ሠራ። ባሕሩ ክብ ቅርጽ የነበረው ሲሆን ከአንዱ ጠርዝ እስከ ሌላኛው ጠርዝ 10 ክንድ፣ ከፍታው ደግሞ 5 ክንድ ነበር፤ መጠነ ዙሪያውም በመለኪያ ገመድ ሲለካ 30 ክንድ ሆነ።+ 3  በባሕሩም ዙሪያ ከሥሩ በእያንዳንዱ ክንድ ላይ በቅል+ ቅርጽ የተሠሩ አሥር ጌጦች ነበሩ። ቅሎቹም ከባሕሩ ጋር አንድ ወጥ ሆነው በሁለት ረድፍ ቀልጠው ተሠርተው ነበር። 4  ባሕሩ 3ቱ ወደ ሰሜን፣ 3ቱ ወደ ምዕራብ፣ 3ቱ ወደ ደቡብ እንዲሁም 3ቱ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ ፊታቸውን ባዞሩ 12 በሬዎች+ ላይ ተቀምጦ ነበር፤ ባሕሩም ላያቸው ላይ ነበር፤ የሁሉም ሽንጥ ወደ መሃል ገባ ያለ ነበር። 5  የውኃ ማጠራቀሚያው ውፍረት አንድ ጋት* ነበር፤ ጠርዙ የጽዋ ከንፈር ይመስል የነበረ ሲሆን በአበባ ቅርጽ የተሠራ ነበር። የውኃ ማጠራቀሚያው 3,000 የባዶስ መስፈሪያ* መያዝ ይችላል። 6  በተጨማሪም ለመታጠቢያ የሚሆኑ አሥር የውኃ ገንዳዎች ሠርቶ አምስቱን በስተ ቀኝ፣ አምስቱን ደግሞ በስተ ግራ አስቀመጣቸው።+ ገንዳዎቹን የሚቃጠለውን መባ+ ለማቅረብ የሚያገለግሉትን ነገሮች ለማጠብ ይጠቀሙባቸው ነበር። ባሕሩ ግን የካህናቱ መታጠቢያ ነበር።+ 7  ከዚያም በተሰጠው መመሪያ መሠረት+ አሥር የወርቅ መቅረዞችን+ ሠርቶ በቤተ መቅደሱ ውስጥ አምስቱን በስተ ቀኝ፣ አምስቱን ደግሞ በስተ ግራ አስቀመጣቸው።+ 8  በተጨማሪም አሥር ጠረጴዛዎችን ሠርቶ በቤተ መቅደሱ ውስጥ አምስቱን በስተ ቀኝ፣ አምስቱን በስተ ግራ አስቀመጣቸው፤+ ከዚያም 100 ጎድጓዳ የወርቅ ሳህኖችን ሠራ። 9  ከዚያም የካህናቱን+ ግቢ+ እንዲሁም ትልቁን ግቢና+ የግቢውን በሮች ሠራ፤ የግቢዎቹንም በሮች በመዳብ ለበጣቸው። 10  ባሕሩንም በስተ ቀኝ በኩል፣ በስተ ደቡብ ምሥራቅ አቅጣጫ አስቀመጠው።+ 11  በተጨማሪም ኪራም አመድ ማጠራቀሚያዎቹን፣ አካፋዎቹንና ጎድጓዳ ሳህኖቹን ሠራ።+ ኪራምም በእውነተኛው አምላክ ቤት ለንጉሥ ሰለሞን ያከናውን የነበረውን ሥራ ጨረሰ፤+ 12  ሁለቱን ዓምዶች፣+ በሁለቱ ዓምዶች አናት ላይ የነበሩትን የጎድጓዳ ሳህን ቅርጽ ያላቸው የዓምድ ራሶች፣ በዓምዶቹ አናት ላይ የነበሩትን የጎድጓዳ ሳህን ቅርጽ ያላቸውን ሁለቱን ክብ የዓምድ ራሶች የሚያስጌጡትን ሁለት መረቦች፣+ 13  ለሁለቱ መረቦች የተሠሩትን 400 ሮማኖች+ ማለትም በዓምዶቹ አናት ላይ የነበሩትን የጎድጓዳ ሳህን ቅርጽ ያላቸውን ሁለት የዓምድ ራሶች ለማስጌጥ የተሠሩትን በእያንዳንዱ መረብ ላይ በሁለት ረድፍ የተደረደሩትን ሮማኖች፣+ 14  አሥሩን ጋሪዎችና* በጋሪዎቹ ላይ የነበሩትን አሥር የውኃ ገንዳዎች፣+ 15  ባሕሩንና ከሥሩ የነበሩትን 12 በሬዎች፣+ 16  አመድ ማጠራቀሚያዎቹን፣ አካፋዎቹን፣ ሹካዎቹንና+ ከዚህ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ዕቃዎች ሁሉ ኪራምአቢቭ+ ለይሖዋ ቤት መገልገያ እንዲሆኑ ለንጉሥ ሰለሞን ከተወለወለ መዳብ ሠራ። 17  ንጉሡ እነዚህ ነገሮች በዮርዳኖስ አውራጃ፣ በሱኮትና+ በጸሬዳህ መካከል በሚገኝ ስፍራ በሸክላ ጭቃ ውስጥ ቀልጠው እንዲሠሩ አደረገ። 18  ሰለሞን የሠራቸው ዕቃዎች እጅግ ብዙ ነበሩ፤ የመዳቡም ክብደት ምን ያህል እንደሆነ አልታወቀም።+ 19  ሰለሞን ለእውነተኛው አምላክ ቤት መገልገያ የሚሆኑትን የሚከተሉትን ነገሮች+ ሠራ፦ የወርቅ መሠዊያውን፣+ ገጸ ኅብስቱ የሚቀመጥባቸውን+ ጠረጴዛዎች፣+ 20  በመመሪያው መሠረት በውስጠኛው ክፍል ፊት የሚበሩትን ከንጹሕ ወርቅ የተሠሩ መቅረዞችና መብራቶቻቸውን፣+ 21  ከወርቅ ይኸውም እጅግ ከጠራ ወርቅ የተሠሩትን የፈኩ አበቦች፣ መብራቶችና መቆንጠጫዎች፣ 22  ከንጹሕ ወርቅ የተሠሩትን የእሳት ማጥፊያዎች፣ ጎድጓዳ ሳህኖች፣ ጽዋዎችና መኮስተሪያዎች እንዲሁም ከወርቅ የተሠሩትን የቤቱን መግቢያ፣ የቅድስተ ቅዱሳኑን+ የውስጥ በሮችና የቤተ መቅደሱን ቤት በሮች።+

የግርጌ ማስታወሻዎች

ወይም “ውኃ ማጠራቀሚያውን።”
አንድ ጋት 7.4 ሴንቲ ሜትር ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
አንድ ባዶስ 22 ሊትር ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ወይም “የውኃ መጫኛ ጋሪዎችና።”