ሁለተኛ ዜና መዋዕል 22:1-12

  • አካዝያስ በይሁዳ ላይ ነገሠ (1-9)

  • ጎቶልያ በጉልበት ዙፋን ላይ ወጣች (10-12)

22  ከዚያም የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች የመጨረሻ ልጁን አካዝያስን* በእሱ ምትክ አነገሡት፤ ከዓረቦቹ ጋር ወደ ሰፈሩ የመጡት ወራሪዎች ታላላቆቹን በሙሉ ገድለዋቸው ነበር።+ በመሆኑም የኢዮራም ልጅ አካዝያስ የይሁዳ ንጉሥ ሆኖ መግዛት ጀመረ።+ 2  አካዝያስ በነገሠ ጊዜ ዕድሜው 22 ዓመት ነበር፤ በኢየሩሳሌምም ሆኖ አንድ ዓመት ገዛ። እናቱም ጎቶልያ+ የተባለች የኦምሪ+ የልጅ ልጅ* ነበረች። 3  እናቱ ክፉ ነገር እንዲያደርግ ትመክረው ስለነበር እሱም የአክዓብን+ ቤት መንገድ ተከተለ። 4  ከአባቱ ሞት በኋላ የአክዓብ ቤት ሰዎች አማካሪዎቹ በመሆን ወደ ጥፋት ስለመሩት ልክ እንደ አክዓብ ቤት እሱም በይሖዋ ፊት መጥፎ የሆነውን ነገር ማድረጉን ቀጠለ። 5  እሱም የእነሱን ምክር ተከትሎ ከሶርያ ንጉሥ ከሃዛኤል+ ጋር በራሞትጊልያድ+ ለመዋጋት ከእስራኤል ንጉሥ ከአክዓብ ልጅ ከኢዮራም ጋር ሄደ፤ በዚያም ቀስተኞች ኢዮራምን አቆሰሉት። 6  እሱም ከሶርያ ንጉሥ ከሃዛኤል ጋር በተዋጋበት ጊዜ+ በራማ ካቆሰሉት ቁስል ለማገገም ወደ ኢይዝራኤል+ ተመለሰ። የይሁዳ ንጉሥ የኢዮራም+ ልጅ አካዝያስ* የአክዓብ ልጅ ኢዮራም+ ቆስሎ*+ ስለነበር እሱን ለማየት ወደ ኢይዝራኤል ወረደ። 7  ይሁንና አካዝያስ ወደ ኢዮራም በመምጣቱ አምላክ ለውድቀት ዳረገው፤ እዚያ ከደረሰ በኋላም ከኢዮራም ጋር የኒምሺን የልጅ ልጅ* ኢዩን+ ለማግኘት ሄዱ፤ ኢዩ የአክዓብን ቤት እንዲያጠፋ ይሖዋ የቀባው ሰው ነበር።+ 8  ኢዩም በአክዓብ ቤት ላይ የተላለፈውን ፍርድ ማስፈጸም ሲጀምር የአካዝያስ አገልጋዮች የነበሩትን የይሁዳን መኳንንትና የአካዝያስን ወንድሞች ልጆች አግኝቶ ገደላቸው።+ 9  ከዚያም አካዝያስን ለመፈለግ ሄደ፤ እነሱም በሰማርያ ተደብቆ ሳለ ያዙት፤ ወደ ኢዩም አመጡት። ከዚያም ገደሉት፤ ይሁንና “ይሖዋን በሙሉ ልቡ የፈለገው የኢዮሳፍጥ የልጅ ልጅ ነው” በማለት ቀበሩት።+ ከአካዝያስ ቤት የመንግሥቱን ሥልጣን የመያዝ ብቃት ያለው ሰው አልነበረም። 10  የአካዝያስ እናት ጎቶልያ+ ልጇ መሞቱን ባየች ጊዜ ተነስታ የይሁዳን ንጉሣውያን ቤተሰብ* በሙሉ አጠፋች።+ 11  ይሁንና የንጉሡ ልጅ የሆነችው ዮሳቤት ሊገደሉ ከነበሩት የንጉሡ ልጆች መካከል የአካዝያስን ልጅ ኢዮዓስን+ ሰርቃ በመውሰድ እሱንና ሞግዚቱን በውስጠኛው መኝታ ክፍል አስቀመጠቻቸው። የንጉሥ ኢዮራም+ ልጅ የሆነችው ዮሳቤት (የካህኑ ዮዳሄ+ ሚስትና የአካዝያስ እህት ነበረች) ከጎቶልያ ደብቃ አቆየችው፤ በመሆኑም ጎቶልያ ሳትገድለው ቀረች።+ 12  እሱም ከእነሱ ጋር ለስድስት ዓመት በእውነተኛው አምላክ ቤት ተደብቆ ቆየ፤ በዚህ ጊዜ ጎቶልያ በምድሪቱ ላይ ትገዛ ነበር።

የግርጌ ማስታወሻዎች

በ2ዜና 21:17 ላይ ኢዮዓካዝ ተብሎም ተጠርቷል።
ቃል በቃል “ሴት ልጅ።”
ወይም “ታሞ።”
በአንዳንድ የዕብራይስጥ ጥንታዊ ቅጂዎች ላይ አዛርያስ ተብሎም ተጠርቷል።
ቃል በቃል “ወንድ ልጅ።”
ቃል በቃል “የመንግሥት ዘር።”