መዝሙር 22:1-31
ለሙዚቀኞች ቡድን መሪ፤ “በንጋት እንስት ርኤም።”* የዳዊት ማህሌት።
22 አምላኬ፣ አምላኬ ለምን ተውከኝ?+
እኔን ከማዳን፣ ከደረሰብኝም ሥቃይ የተነሳ የማሰማውን ጩኸት+ ከመስማትየራቅከው ለምንድን ነው?
2 አምላኬ ሆይ፣ በቀን ደጋግሜ እጣራለሁ፤ አንተ ግን አትመልስልኝም፤+በሌሊትም ዝም ማለት አልቻልኩም።
3 አንተ ግን ቅዱስ ነህ፤+እስራኤል በሚያቀርበው ውዳሴ ተከበሃል።*
4 አባቶቻችን እምነታቸውን በአንተ ላይ ጣሉ፤+በአንተ ተማመኑ፤ አንተም ሁልጊዜ ትታደጋቸው ነበር።+
5 ወደ አንተ ጮኹ፤ ደግሞም ዳኑ፤በአንተ ተማመኑ፤ የጠበቁት ሳይፈጸም ቀርቶም አላዘኑም።*+
6 እኔ ግን ትል እንጂ ሰው አይደለሁም፤ሰው ያፌዘብኝ፣* ሕዝብም የናቀኝ ነኝ።+
7 የሚያዩኝ ሁሉ ያላግጡብኛል፤+በንቀትና በፌዝ ጭንቅላታቸውን እየነቀነቁ እንዲህ ይሉኛል፦+
8 “ራሱን ለይሖዋ በአደራ ሰጥቷል። እስቲ እሱ ይታደገው!
በእሱ እጅግ የተወደደ ስለሆነ እሱ ያድነው!”+
9 ከማህፀን ያወጣኸኝ አንተ ነህ፤+በእናቴ ጡት ተማምኜ እንድኖር ያደረግከኝ አንተ ነህ።
10 ስወለድ ጀምሮ ለአንተ በአደራ ተሰጠሁ፤*ከእናቴ ማህፀን ጀምሮ አንተ አምላኬ ነህ።
11 ችግር ሊደርስብኝ ስለሆነ ከእኔ አትራቅ፤+ደግሞም ሌላ ረዳት የለኝም።+
12 ብዙ ወይፈኖች ከበውኛል፤+የባሳን ኃይለኛ ኮርማዎችም በዙሪያዬ ናቸው።+
13 ያደነውን እንደሚቦጫጭቅ የሚያገሳ አንበሳ+አፋቸውን በእኔ ላይ ከፈቱ።+
14 እንደ ውኃ ፈሰስኩ፤አጥንቶቼ ሁሉ ከመጋጠሚያቸው ወለቁ።
ልቤ እንደ ሰም ሆነ፤+በውስጤም ቀለጠ።+
15 ኃይሌ እንደ ገል ደረቀ፤+ምላሴ ከላንቃዬ ጋር ተጣበቀ፤+እንድሞትም ወደ ጉድጓድ አወረድከኝ።+
16 ውሾች ከበውኛልና፤+እንደ ክፉ አድራጊዎች ሸንጎ በዙሪያዬ ሰፍረዋል፤+እንደ አንበሳ ሆነው እጆቼና እግሮቼ ላይ ተረባረቡ።*+
17 አጥንቶቼን ሁሉ መቁጠር እችላለሁ።+
እነሱም አዩኝ፤ ትኩር ብለውም ተመለከቱኝ።
18 መደረቢያዎቼን እርስ በርሳቸው ተከፋፈሉ፤በልብሴም ላይ ዕጣ ተጣጣሉ።+
19 አንተ ግን ይሖዋ ሆይ፣ ከእኔ አትራቅ።+
አንተ ብርታቴ ነህ፤ እኔን ለመርዳት ፍጠን።+
20 ከሰይፍ አድነኝ፤*ውድ ሕይወቴን* ከውሾች መዳፍ* ታደጋት፤+
21 ከአንበሳ አፍና ከዱር በሬዎች ቀንድ አድነኝ፤+መልስ ስጠኝ፤ ታደገኝም።
22 ስምህን ለወንድሞቼ አሳውቃለሁ፤+በጉባኤ መካከልም አወድስሃለሁ።+
23 እናንተ ይሖዋን የምትፈሩ፣ አወድሱት!
እናንተ የያዕቆብ ዘር ሁሉ፣ ከፍ ከፍ አድርጉት!+
እናንተ የእስራኤል ዘር ሁሉ፣ ለእሱ ታላቅ አክብሮት አሳዩ።
24 እሱ የተጨቆነውን ሰው መከራ አልናቀምና፤+ ደግሞም አልተጸየፈም፤ፊቱን ከእሱ አልሰወረም።+
ለእርዳታ ወደ እሱ በጮኸ ጊዜ ሰምቶታል።+
25 በታላቅ ጉባኤ መካከል አወድስሃለሁ፤+እሱን በሚፈሩት ፊት ስእለቴን እፈጽማለሁ።
26 የዋሆች በልተው ይጠግባሉ፤+ይሖዋን የሚፈልጉት እሱን ያወድሱታል።+
ለዘላለም ተደስታችሁ ኑሩ።*
27 የምድር ዳርቻዎች ሁሉ ይሖዋን አስታውሰው ወደ እሱ ይዞራሉ።
የሕዝቦች ነገዶች ሁሉ በፊትህ ይሰግዳሉ።+
28 ንግሥና የይሖዋ ነውና፤+ብሔራትን ይገዛል።
29 በምድር ያሉ ባለጸጎች ሁሉ* ይበላሉ፤ ይሰግዳሉም፤ወደ አፈር የሚወርዱ ሁሉ በእሱ ፊት ይንበረከካሉ፤ከእነሱ መካከል አንዳቸውም ሕይወታቸውን* ማቆየት አይችሉም።
30 ዘሮቻቸው ያገለግሉታል፤መጪው ትውልድ ስለ ይሖዋ ይነገረዋል።
31 መጥተው ጽድቁን ያወራሉ።
ገና ለሚወለድ ሕዝብ ያደረገውን ነገር ይናገራሉ።
የግርጌ ማስታወሻዎች
^ ቅኝት ወይም የሙዚቃ ስልት ሊሆን ይችላል።
^ ወይም “እስራኤል በሚያቀርበው ውዳሴ መካከል (ላይ) ነግሠሃል።”
^ ወይም “ኀፍረት አልደረሰባቸውም።”
^ ወይም “የነቀፈኝ።”
^ ቃል በቃል “በአንተ ላይ ተጣልኩ።”
^ ወይም “እጆቼንና እግሮቼን ቸነከሩ።”
^ ወይም “ነፍሴን ከሰይፍ አድናት።”
^ ቃል በቃል “አንድ ያለችኝን።” ነፍሱን ወይም ሕይወቱን ያመለክታል።
^ ቃል በቃል “እጅ።”
^ ቃል በቃል “ልባችሁ ለዘላለም ይኑር።”
^ ቃል በቃል “የሰቡት ሁሉ።”
^ ወይም “ነፍሳቸውን።”