በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 117

የጌታ ራት

የጌታ ራት

ማቴዎስ 26:21-29 ማርቆስ 14:18-25 ሉቃስ 22:19-23 ዮሐንስ 13:18-30

  • ይሁዳ ከሃዲ መሆኑ ተገለጸ

  • ኢየሱስ የመታሰቢያ በዓል አቋቋመ

በዚህ ምሽት ኢየሱስ የሐዋርያቱን እግር በማጠብ ስለ ትሕትና አስተምሯቸዋል። ፋሲካን ከበሉ በኋላ ሳይሆን አይቀርም ኢየሱስ፣ ዳዊት የተናገረውን ትንቢት በመጥቀስ እንዲህ አለ፦ “ከእኔ ጋር ሰላም የነበረው፣ እምነት የጣልኩበትና ከማዕዴ ይበላ የነበረ ሰው ተረከዙን በእኔ ላይ አነሳ።” ኢየሱስ አክሎም “ከእናንተ አንዱ አሳልፎ ይሰጠኛል” ሲል በግልጽ ተናገረ።—መዝሙር 41:9፤ ዮሐንስ 13:18, 21

ሐዋርያቱ እርስ በርስ ተያዩ፤ ከዚያም እያንዳንዳቸው “ጌታ ሆይ፣ እኔ እሆን?” ይሉት ጀመር። የአስቆሮቱ ይሁዳ እንኳ ይህን ጥያቄ አቀረበ። ጴጥሮስ፣ ይህ ግለሰብ ማን እንደሆነ እንዲያጣራ በማዕዱ ላይ ከኢየሱስ አጠገብ የተቀመጠውን ዮሐንስን ጠየቀው። እሱም ወደ ኢየሱስ ደረት ጠጋ ብሎ “ጌታ ሆይ፣ ማን ነው?” አለው።—ማቴዎስ 26:22፤ ዮሐንስ 13:25

ኢየሱስም “ይህን የማጠቅሰውን ቁራሽ ዳቦ የምሰጠው ሰው ነው” ሲል መለሰ። ከዚያም ዳቦውን የቀረበው ሳህን ውስጥ አጥቅሶ ለይሁዳ ከሰጠው በኋላ እንዲህ አለ፦ “የሰው ልጅ ስለ እሱ በተጻፈው መሠረት ይሄዳል፤ የሰውን ልጅ አሳልፎ ለሚሰጠው ለዚያ ሰው ግን ወዮለት! ያ ሰው ባይወለድ ይሻለው ነበር።” (ዮሐንስ 13:26፤ ማቴዎስ 26:24) በዚህ ጊዜ ይሁዳ ሰይጣን ገባበት። አስተሳሰቡ የተበላሸው ይህ ሰው የዲያብሎስን ዓላማ ለመፈጸም ፈቃደኛ በመሆኑ ‘የጥፋት ልጅ’ ሆነ።—ዮሐንስ 6:64, 70፤ 12:4፤ 17:12

ኢየሱስ ይሁዳን “እያደረግከው ያለኸውን ነገር ቶሎ አድርገው” አለው። ሌሎቹ ሐዋርያት፣ የገንዘብ ሣጥኑን የሚይዘው ይሁዳ “ለበዓሉ የሚያስፈልጉትን ነገሮች እንዲገዛ ወይም ለድሆች የሆነ ነገር እንዲሰጥ ኢየሱስ ያዘዘው” መሰላቸው። (ዮሐንስ 13:27-30) ይሁዳ ግን ኢየሱስን አሳልፎ ለመስጠት ሄደ።

ፋሲካ በተከበረበት በዚሁ ምሽት ላይ ኢየሱስ ሌላ አዲስ በዓል አቋቋመ። አንድ ቂጣ ወስዶ የምስጋና ጸሎት ካቀረበ በኋላ ቆራርሶ ሐዋርያቱ እንዲበሉት ሰጣቸው። ከዚያም “ይህ ስለ እናንተ የሚሰጠውን ሥጋዬን ያመለክታል። ይህን ሁልጊዜ ለመታሰቢያዬ አድርጉት” አላቸው። (ሉቃስ 22:19) ሐዋርያቱም ቂጣውን እየተቀባበሉ በሉ።

ቀጥሎም ኢየሱስ የወይን ጠጅ የያዘውን ጽዋ አንስቶ የምስጋና ጸሎት ካቀረበ በኋላ ሰጣቸው። ሁሉም ከእሱ ጠጡ። ኢየሱስ የወይን ጠጁን አስመልክቶ እንዲህ አለ፦ “ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው ደሜ አማካኝነት የሚመሠረተውን አዲሱን ቃል ኪዳን ያመለክታል።”—ሉቃስ 22:20

በዚህ መንገድ ኢየሱስ፣ ተከታዮቹ በየዓመቱ ኒሳን 14 ላይ የሞቱን መታሰቢያ እንዲያከብሩ መመሪያ ሰጠ። ይህ በዓል፣ እምነት ያላቸው የሰው ልጆች ከኃጢአትና ከሞት ኩነኔ ነፃ እንዲወጡ ኢየሱስና አባቱ ያደረጉትን ዝግጅት ለማስታወስ ይረዳል። እርግጥ ነው፣ ፋሲካ ለአይሁዳውያን ነፃ መውጣትን ያመለክት ነበር፤ የመታሰቢያው በዓል ግን እምነት ያላቸው የሰው ልጆች በሙሉ ከዚያ የላቀ እውነተኛ ነፃነት እንደሚያገኙ ተስፋ ይሰጣል።

ኢየሱስ፣ ደሙ “ስለ ብዙዎች ለኃጢአት ይቅርታ” እንደሚፈስ ተናገረ። እንዲህ ያለ ይቅርታ ከሚያገኙት በርካታ ሰዎች መካከል ታማኝ ሐዋርያቱና ሌሎች ታማኝ ደቀ መዛሙርት ይገኙበታል። በአባቱ መንግሥት ከእሱ ጋር የሚሆኑት እነዚህ ሰዎች ናቸው።—ማቴዎስ 26:28, 29